በብዙ መቶሺዎች የሚቆጠሩ ሙስሊሞች ተቃውሞአቸውን ሲያሰሙ ዋሉ

የካቲት ፩ (አንድ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-<<ጅሀዳዊ ሀረካት>> የተሰኘውንና በ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሰሞኑን የተላለፈውን ፊልም በመቃወምና ለታሰሩት የሙስሊም መፍትሔ =  አፈላ ላጊ ኮሚቴዎች አጋርነታቸውን ለመግለጽ በብዙ መቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሙስሊሞች ዛሬ ከፍተኛ ተቃውሞ ሲያሰሙ ውለዋል።

“መሪዎቻችን ይፈቱ! ዓላማችን ኢስላማዊ መንግስት ሳይሆን የሀይማኖት ነፃነታችንን ማግኘት ነው! ድምፃችን ይሰማ ፣ በዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ላይ የሚደርሰው ጥቃት ይቁም>>የሚሉ እንዲሁም የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንን የሚያወግዙ መፈክሮች ቀርበዋል።

በተቃውሞው ላይ የተሳተፈ አንድ ሙስሊም፣  ተቃውሞው መስሊሙ ለመሪዎቹ ያለውን ድጋፍ በቁርጠኝነት የገለጠበት ነበር ብሎአል።

<<ጅሀዳዊ ሀረካት>>በሚል ርዕስ በ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የተለቀቀው የፈጠራ ድራማ በሙስሊሞች ብቻ ሳይሆን በሌሎች እምነት ተከታዮች፣በተቃዋሚ ፓርቲዎች እና በሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ጭምር ከፍ ያለ ተቃውሞና ውግዘት እየቀረበበት ይገኛል።