በቤንሻንጉል 54 የክልሉ ባለስልጣናት ታሰሩ

(ኢሳት ዲሲ–ሰኔ 26/2010) በቤንሻንጉል ክልል ከተከሰተውና 14 ያህል ሰዎች ከተገደሉበት ግጭት ጋር በተያያዘ 54 የክልሉ ባለስልጣናት መታሰራቸው ታወቀ።

የፖሊስ ኮሚሽነሩ ከሥልጣናቸው እና ከስራቸው ሲታገዱ አስራ አንድ ፖሊሶች ታስረዋል።

የቤንሻንጉል ክልል ፕሬዝዳንት እንዳስታወቁት የክልሉ ልዩ ሃይል ፖሊስ ሃላፊዎችም ከስልጣን ተባረዋል ።

የቤንሻንጉል  ክልል ፕሬዝዳንት አቶ አሻድሊ ሁሴን ለመንግስት መገናኛ ብዙሃን እንደገለጹት ከተፈጠረው ችግር ጋር በተያያዘ በአንዳንድ አካባቢዎች  መንገዶች እንደተዘጉ ይገኛሉ ፣ሆኖም በአሶሳ ከተማ የዕለተ ዕለት መደበኛ እንቅስቃሴ በመመለስ  ላይ መሆኑን አመልክተዋል።

ከግጭቱ ጋር በተያያዘ የክሉ ፖሊስ ኮሚሽነር እንዲሁም የክልሉ የአስተዳደር እና ጸጥታ ዘርፍ ሃላፊ  ከስራቸው ሲታገዱ ፣ 11 ፖሊሶች ደግሞ ተባረዋል።

የልዩ ሃይል ፖሊስ መምሪያ ሃላፊዎች ደግሞ ከስልጣናቸው ተባረዋል።

በግጭቱ 14 ሰዎች ሲገደሉ፣70 ያህል መቁሰላቸውንም ከቤንሻንጉል ክልል ፕሬዝዳንት  ከአቶ አሻድሊ ሃሰን መግለጫ መረዳት ተችሏል።

የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን አስተዳዳር በመቃወም ላይ ያሉት ከሂደቱ የወጡ ሃይሎች ግጭቶችን በማቀነባበር እየተወነጀሉ ይገኛሉ።

የአዋሳውን ግጭት ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በሰጡት መግለጫ ግጭቱን የሚያቀነባብሩትን ሃይሎች የቀን ጅቦች ሲሉ መጥቀሳቸው ይታወሳል።

አሁንም በየክልሉ በተለይም በዳር ሃገር ጸጉረ ልውጦችን ሕብረተሰቡ እንዲከታተል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ትናንት ጥሪ አቅርበዋል።