በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከሚያዚያ አጋማሽ ጀምሮ ባሉት ቀናት ከ5 በላይ የአማራ ተወላጆች በአሰቃቂ ሁኔታ ተገደሉ

በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከሚያዚያ አጋማሽ ጀምሮ ባሉት ቀናት ከ5 በላይ የአማራ ተወላጆች በአሰቃቂ ሁኔታ ተገደሉ
(ኢሳት ዜና ግንቦት 10 ቀን 2010 ዓ/ም) ለአመታት በክልሉ በኖሩ የአማራ ተወላጆች ላይ የሚደርሰው ጥቃት ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ መምጣቱን የሚገልጹት የአማራ ተወላጆች፣ ባለፉት 2 ሳምንታት ብቻ ከ5 ያላነሱ ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ ተገድለዋል ብለዋል።
ደባጢ ወረዳ ውስጥ የ14 አመት ታዳጊ የሆነው አበጠር ወርቁ እጅግ አሰቃቂ በሆነ ሁኔታ ተደብድቦና ብልቱ ተቆርጦ ከተገኘ በሁዋላ ለህክምና ከፓዊ ወደ ባህርዳር ፈለገ ህይወት ሆስፒታል ተወስዷል። በማምቡክ ወረዳ ደግሞ ሁለት የቋሪት ተወላጆች ባልና ሚስት በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውን ሚያዚያ 30 ቀን መቀበራቸውን፣ በአጠቃላይ ከሚያዚያ 16 ጀምሮ 5 ሰዎች ጥቃት ተፈጽሞባቸው 4 ቱ ሲሞቱ አንዱ በህክምና ላይ ነው።
የቤንሻንጉል ጉሙዝ ባለስልጣናት በታዳጊ ወጣት አበጥር ላይ አሰቃቂ ድርጊት የፈጸሙት ሰዎች መያዛቸውን መግለጹን የአማራ ክልል የመገናኛ ብዙሃን ዘግቧል።
የአማራ ተወላጆች ጥቃቱ የተፈጸመባቸው በአማራነታቸው የተወሰደ ነው ወይም ከባህላቸው ጋር በተያያዘ ነው ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ተፈናቃዮች ሲመልሱ፣ እስከዛሬ ባለው እውነታ ጥቃት የሚፈጸመው በአማራ ላይ ብቻ መሆኑን አማራው እረኛ በማጣቱ የጥቃት ሰለባ መሆኑን ተናግረዋል።
ከክልሉ ተፈናቅለው በባህርዳር ከተማ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ተጠልለው የሚገኙ የአማራ ተወላጆች አሁንም መፍትሄ አላገኙም። ተፈናቃዮቹ ወደ መጡበት እንዲመለሱ በብአዴንና በክልሉ ባለስልጣናት የተናገራቸው ቢሆንም፣ ተፈናቃዮቹ ግን በክልላቸው በገጠር ወይም በከተማ እንዲያስፍራቸው፣ ሃብታቸውን ከዘረፈው የቤንሻንጉል ጉሙዝ ንብረታችንን እንዲያስመልሱላቸውና የራሳቸውን አማራጭ እንደሚወስዱ ተናግረዋል።
በክልሉ መንግስትና በተፈናቃዮች መካከል አለመግባባት መፈጠሩን የሚናገሩት ተፈናቃዮች፣ መንግስት አንድም ቀን እንዳልረዳቸው እርዳታ የሚለግሱዋቸው የባህርዳር ህዝብና በውጭ አገር የሚገኙ ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ተናግረዋል።