በቤንሻንጉል በቁጥጥር ስር የዋሉ ግለሰቦች ቁጥር 62 ደረሰ

(ኢሳት ዲሲ–ግንቦት 1/2011) በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል መተከል ዞን በማምቡክና አከባቢው ከተከሰተው ግጭት ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ስር የዋሉ ግለሰቦች ቁጥር 62 መድረሱ ተገለጸ።

የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን እንዳስታወቀው በማምቡክ 50 በጃዊ ደግሞ 12 ሰዎች ተይዘው ምርመራ እየተደረገባቸው ነው።

ፋይል

ኮሚሽኑ ጨምሮ እንደገለጸው በአሁኑ ወቅት በአከባቢዎቹ ሰላምና መረጋጋት ሰፍኗል።

ተቋርጠው የነበረው የትራንፖርት አገልጎሎትም መጀመሩን ኮሚሽኑ አስታውቋል።

የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አድጎ አምሳያ በጃዊው ጥቃት 200 ሰዎች ተገድለዋል ሲሉ ለሪፖርተር ገልጸዋል።

በጥቃቱ ምክንያት የተፈናቀሉት ሰዎች ቁጥርም 4ሺህ ደርሷል ብለዋል ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ያነጋገራቸው የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ፖሊስ ኮሚሽነር እንደገለጹት በሁለት አካባቢዎች የተነሱትን ግጭቶች በመቆስቆስና በማባባስ እጃቸው አለበት የተባሉ ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር የማዋሉ እንቅስቃሴ በስፋት ቀጥሏል።

በእስከአሁንም 62 ሰዎች ተይዘው ምርመራ እየተደረገባቸው ነው። በተጠርጣሪዎች ላይ ማስረጃ የማሰባሰብ ሥራው መቀጠሉንም አስታውቀዋል፡፡

በክልሉ መተከል ዞን በማምቡክና በአከባቢው ግጭቶች እንዲፈጠሩ ማድረጋቸውና በሂደትም መረጋጋት እንዳይፈጠር በማባባስ የሚጠረጠሩ ግለሰቦች በርካታ መሆናቸውን የገለጹት ኮሚሽነሩ በቀጣይም ሌሎችን በመያዝ ለፍርድ የማቅረቡ ተግባር ይካሄዳል ብለዋል።

ከማምቡክ ሌላ በጃዊ ወረዳ ከተፈጠረው ግጭት ጋር በተያያዘ እጃቸው ያለበት ሰዎች ተለይተው ምርመራ እየተደርገባቸው ሲሆን 12 ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለዋል ብለዋል።

በማምቡክ ከተያዙት 50 ግለሰቦች ጋር በድምሩ 62 ሰዎች ለፍርድ እንዲቀርቡ የሚደረግ እንደሚሆን ነው ኮሚሽነሩ ገለጸዋል።

በፌዴራል እና በክልል ፖሊስ የተደራጀው ግጭቱን የሚመረምረው ቡድን ስራውን አጠናክሮ መቀጠሉን ኮሚሽነሩ ጠቅሰዋል፡፡

ኮሚሽነሩ አቶ መሀመድ ሀምዲል እንዳሉት በአማራና ቤንሻንጉል ጉምዝ ክልሎችና በመከላከያ ሰራዊቱ ትብብር በተደረገ ጸጥታ የማስከበር እርምጃ ግጭት የተከሰተባቸው አከባቢዎች ወደ መረጋጋት ተመልሰዋል።

በግጭቱ ምክንያት ተቋርጦ የነበረው የአሶሳ- ግልገል በለስ፣ የግለገል በለስ- ማምቡክ፣ የግልገል በለስ-ፓዌ-ጃዊ-ማንኩሽና እና ሌሎችም ከተሞች የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት መጀመሩንም አቶ መሀመድ ገልጸዋል።

በቅርቡ የምርመራ ቡድኑ 200 የሚጠጉ የቀስት ደጋን ከነመወርወሪያው፣ ገጀራ እና መጥረቢያ በቁጥጥር ስር ማዋሉን ኮሚሽነሩ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

በማምቡክና አካባቢው ግጭት የ21 ሰዎች ህይወት ማለፉን መረጃዎች ያመለክታሉ።

በሌላ በኩል በጃዊ ወረዳ በተፈጸመ ጥቃት 200 ሰዎች መገደላቸውን የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት ገልጸዋል።

ምክትል ፕሬዝዳንቱ አቶ አድጎ አምሳያ ለሪፖርተር እንደገለጹት የእኛ ወገን ተነካ በሚል በተፈጸመ ጥቃት ከ200 በላይ ሰዎች ተገድለዋል።

ጃዊን ጨምሮ ከተለያዩ አካባቢዎች ተፈናቅለው በመጠለያ የሚገኙ ሰዎች ከ4,000 በላይ እንደሆኑም ገልጸዋል፡፡

በመጠለያ ጣቢያዎች ወላጆቻቸውን ያጡ በርካታ ሕፃናት እንደሚገኙም ምክትል ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል፡፡

አሁን ሁኔታዎች ተረጋግተዋል። ስጋት ያለባቸውን አከባቢዎች በመለየት ጸጥታ የማስከበሩን ስራ በተቀናጀ መልኩ እየሰራን ነው ማለታቸውን ሪፖርተር ዘግቧል።