በቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ የተከሰሱት ሰዎች የፍርድ ውሳኔ ተላለፈ

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 3/2010) በቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ የተከሰሱት የ38ቱ ሰዎች የፍርድ ውሳኔ ለሌላ ጊዜ ተላለፈ።

ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ለሌላ ጊዜ ያስተላለፈው በስራ መብዛት እና ሰንዶችን መርምሬ ባለመጨረሴ ነው ብሏል።

በእነ ማስረሻ ሰጤ መዝገብ ዶክተር ፍቅሩ ማሩን ጨምሮ 38 ተከሳሾች በፍርድቤቱ ቀነ ቀጠሮ መራዘም ያላቸውን ቅሬታ መግለጻቸው ተነግሯል።

በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት በቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ የተከሰሱ ሰዎችን በተመለከተ አቃቤ ሕግ ያቀረባቸውን ምስክሮች ሲሰማ ነበር የቆየው።

ፍርድ ቤቱ አቃቤ ሕግ ካቀረባቸው 85 ምስክሮችን የ48ቱን በመቀበል የሌሎቹን 28 ግን ውድቅ ማድረጉም ይታወሳል።

የአቃቤ ሕግ ምስክሮቹ በተከሳሾቹ ላይ ቢመሰክሩም ፣የመሰከሩባቸውን ሰዎች ማንነት አለማወቃቸውን  ፍርድ ቤቱ ገልጾ ነበር።

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን  የ25 ገጽ ሪፖርትን ጨምሮ በተከሳሾች ላይ በቀረበው ማስረጃ መሰረት ፍርድ ቤቱ በ38ቱም ተከሳሾች ላይ  ውሳኔ ይሰጣል ተብሎ ቢጠበቅም በስራ መብዛትና ሰነዶችን መርምሬ አልጨረስኩም በሚል ሰበብ በቀነ ቀጠሮ አልፎታል።

በዚሁም መሰረት በእነ ማስረሻ ሰጤ መዝገብ ዶክተር ፍቅሩ ማሩን ጨምሮ በተከሰሱ 38 ተከሳሾች ላይ የጥፍተኝነትም ሆነ ከክሱ ነጻ ናቸው የሚል ውሳኔ ለመስጠት ለሚያዚያ 20/2010 ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ነው የተነገረው።

በቂሊንጦው ቃጠሎ 23 እስረኞች ሲሞቱ በወቅቱ በአገዛዙ በኩል በተሰጠ መግለጫ 21ዱ በጭስ በመታፈን 2ቱ ደግሞ በእስረኛ ጠባቂዎች መገደላቸው መገለጹ ይታወሳል።

በኋላ ላይ ግን 38 እስረኞች የአርበኞች ግንቦት ሰባትና የኦነግ አባል በመሆን ያደራጁት ቃጠሎ ነው በሚል ክስ መመስረቱ ነው የሚታወቀው።

እናም የቃጠሎው መንስኤና በችግሩ የሞቱት ሰዎች ቁጥር አሁንም አወዛጋቢ እንደሆነ ይገኛል።

በርካታ የአይን ምስክሮች እስረኞቹ በጥይት ተደብደበው እንደተገደሉ ቢናገሩም አገዛዙ ግን ለሞቱት ሰዎች የ38ቱ ሰዎች እጅ አለበት በሚል ክስ መስርቶ አሁንም በሂደት ላይ ይገኛል።