በሱዳን የገዢው ፖርቲ ጽሕፈት ቤት ተቃጠለ

(ኢሳት ዲሲ–ታህሳስ 11/2011)ሱዳን ውስጥ ለተቃውሞ አደባባይየወጡ ወጣቶች የገዢውን ፖርቲ ጽሕፈት ቤት አቃጠሉ።

የተቃውሞው መነሻ በነዳጅ እና በዳቦ ዋጋ ላይ የተደረገው ጭማሪ እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል።

ተቃውሞው የተነሳውና የተቀጣጠለው ከርዕሰ መዲናዋ ካርቱም 320 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው አትባራ በተባለው ከተማ ሲሆን በተቃውሞው የሱዳኑ ገዢ ፓርቲ ናሽናል ኮንግረስ ጽሕፈት ቤት ከመቃጠሉ ባሻገር በጎዳናዎችም ላይ እሳት እያነደደ መገኘቱን አልጀዚራ ዘግቧል።

አንድ የሱዳን ፓውንድ ይሸጥ የነበረው ዳቦ ወደ 3 ፖውንድ ከፍ ማለቱና በተመሳሳይ የነዳጅ ዋጋ እየጨመረ መገኘቱ ለተቃውሞው መነሻ እንደሆነም ተመልክቷል።

ተቃውሞው ከአትባራ ወደ ሬድ ሲት ስቴት መሸጋገሩ የተገለጸ ሲሆን ተቃውሞው የአልባሽር መንግስት ከስልጣን ይውረድ ወደሚል ተሸጋግሯል።

ተቃውሞው በተጠናከረበት አትባራ ከተማና በአጠቃላይ በናይል ሪቨር ስቴት የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ የታወጀ ሲሆን የሰዓት ዕላፊም ተደንግጓል።

ከሰዓት 12 ሰዓት በኋላ መንቀሳቀስ እንደማይቻልም ተደንግጓል።

የ74 ዓመቱ ፕሬዝዳንት ጄኔራል ኦማር አልበሽር በመፈንቅለ መንግስት ስልጣን ከያዙ የፊታችን ሰኔ 30 ዓመት ይሆናቸዋል።