በሰሜን ጎንደር ዞን ጭልጋ ወረዳ ህዝበ ውሳኔ አያስፈልገንም ባሉ አራት ቀበሌዎች በመንግስት ታጣቂዎች ወከባ እየተካሄደ ነው

(ኢሳት ዜና–መስከረም 10/2010)በሰሜን ጎንደር ዞን ጭልጋ ወረዳ ህዝበ ውሳኔ አያስፈልገንም ባሉ አራት ቀበሌዎች በመንግስት ታጣቂዎች ወከባ እየተካሄደ መሆኑ ተገለጸ።

የህወሀት/ብአዴን ካድሬዎች በአራቱ ቀበሌዎች ተሰማርተው ህዝቡን እያስፈራሩት መሆናቸውን ከስፍራው የደረሰን ዜና አመልክቷል።

ባለፈው ዕሁድ በተካሄደውና ከ8ቱ ቀበሌዎች በ7ቱ የህዝብ ድምጽ የተነፈገው የህወሀት ቡድን ቀድም ብለው ህዝበ ውሳኔ አያስፈልገንም ያሉት 4 ቀበሌዎች በቅማንት አስተዳደር ስር እንዲሆኑ ከፍተኛ ጫና በመፍጠር ላይ በመሆኑ በአካባቢው ውጥረቱ ማየሉ ታውቋል።

ከባለፈው ዕሁድ ህዝበ ውሳኔ በኋላ ሰሜን ጎንደር ጭልጋ የወታደራዊ ቀጠና መስሏል ይላሉ ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች።

የህዝቡን ውሳኔ ለመቀልበስና ህዝበ ውሳኔ መደረግ በማያስፈልግባቸው ቀበሌዎች በአስገዳጅነት ለማድረግ የህወሀት መንግስት የሃይል ርምጃን ብቸኛ አማራጭ አድርጎ ወደ አካባቢው ተሰማርቷል።

ለኢሳት የሚደርሱ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ከዕሁዱ ህዝበ ውሳኔ በኋላ ከተገደሉት 4 ሰዎች በተጨማሪ በዛሬው ዕለት ከሸዲ ወደ ሽንፋ በሚወስደው መንገድ ላይ 2 ሰዎች ተገድለው ተገኝተዋል።

ምርጫም አያስፈልገንም ያሉ 4 ቀበሌወች በቅማንት ስም በህወሀት መንግስት በተደራጀው ኮሚቴ አማካኝነት ከፍተኛ ወከባ እየተፈጸመባቸው ይገኛል። እነዚህ የቅማንት ኮሚቴ አባላት በታጣቂዎች ታጅበው በ4ቱ ቀበሌዎች መሰማራታቸው የተገለጸ ሲሆን ህዝበ ውሳኔ አያስፈልገንም ያለውን ህዝብ ለማግባባት በሚል ዛቻ እና ማስፈራሪያ ሲያደርጉ መዋላቸው ታውቋል።

ዛሬ አያስፈልገንም ብትሉ ፌዴሬሽኑ ከወሰነ ምንም አታመጡም። ምርጫ መደረጉ አይቀርም እያሉ ሲዝቱ እንደነበርም በስብሰባው የተገኙ ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

ከባለፈው ሰኞ ጀምሮ ያለውን ውጥረት በተመለከተ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ህወሀት በ4ቱ ቀበሌዎች ህዝበ ውሳኔ ለማድረግ በከፍተኛ ደረጃ እየተንቀሳቀሰ ነው።

በሰሜን ጎንደር ከጎንደር አዘዞ እስከ መተማ ድረስ ባለው መስመር 180 ኪ.ሜ ጨምሮ በውስጥ ዙሪያ ቀበሌዎች እና መንደሮች ውጥረቱ የጨመረ ሲሆን አልፎ አልፎ የተኩስ ድምፆች እንደሚሰሙ የሚደርሱን መረጃዎች ያመልክታሉ።

በጭልጋ ወደ ሸዲ በሚወስደው መንገድ ነጋዴ ባህር ሳይደርስ ግንት ተራራ ላይ የአጋዚ ጦር መስፈሩም ታውቋል።

በሸዲ ጎንደር በር ባለው ወታደራዊ ካምፕ በተጨማሪ በቅርብ ርቀት ባለችው ብርሺኝ ገንዳውሃ አካባቢ ያለው ውጥረት አካባቢውን የጦርነት ቀጠና እንዳስመሰለው ይነገራል።

ከሸዲ ሽንፋ መንገዱ በከፊል የተዘጋ ሲሆን በተወሰኑ ቦታዎች የአጋዚ ጦር እና ታጣቂዎች እንደሚታዩ ተገልጿል።

ከሸዲ መተማ 37 ኪ.ሜ በመሃል ያለችውን ኮኪት ከተማን ጨምሮ ከፍተኛ ውጥረት እንዳለም ይነገራል። መንገዶች ዝግ ናቸው።

በዕሁዱ ህዝበ ውሳኔ አንድነቱን ያስመሰከረው የአማራና የቅማንት ህዝብ በህወሀት በኩል እየመጣ ያለውን ትንኮሳ በጋራ ሆነው እንዲያከሽፉት እየተጠየቀ ነው።

በ4ቀበሌዎች ህዝበ ውሳኔ እንዲካሄድ በህወሀት እየተደረገ ያለው ግፊት ወደ እርስበርስ ግጭት እንዳይወስድ ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበትም የሀገር ሽማግሌዎች ጥሪ በማድረግ ላይ ናቸው።