በርካታ ኢትዮጵያውያን ዛሬም በእስር ቤት እየተሰቃዩ ነው

በርካታ ኢትዮጵያውያን ዛሬም በእስር ቤት እየተሰቃዩ ነው
(ኢሳት ዜና ሰኔ 4 ቀን 2010 ዓ/ም) ዶ/ር አብይ ጠ/ሚኒስትር ሆነው ከተሾሙበት ጊዜ አንስቶ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ አቶ አንዷለም አራጌ፣ ጄ/ል ተፈራ ማሞን፣ አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ ሌሎችም በርካታ የህሊና እስረኞች የተፈቱ ቢሆንም፣ አሁንም ቁጥራቸው ቀላል የማይባል እስረኞች በእስር ቤት እየተሰቃዩ ነው።
ዛሬም ፍትህ ተነፍጓቸው በእስር ላይ ከሚገኙት መካከል ላለፉት 14 ዓመታት በጨለማ እስር ቤት ሲሰቃይ የቆው በዝዋይ እስር ቤት የሚገኘው ካፒቴን በሃይሉ ገብሬ ይገኝበታል። ካፒቴን በሃይሉ በ1997ዓም ምርጫ ወቅት በህዝቡ ላይ የደረሰውን ግድያ በማውገዝ የሚያበረውን ሄሊኮፕተር ይዞ በመጥፋት ጅቡቲ ውስጥ የፖለቲካ ጥገኝነት ከጠየቀ በሁዋላ፣ የጅቡቲ መንግስት አለማቀፍ የስደተኞችን ህግ በመጣስ አሳልፎ የሰጠው ነው።
ላለፉት 5 ዓመታት ከጥፍር መንቀል ጀምሮ ሌሎችም አሰቃቂ ድርጊቶች ሲፈጸሙበት የቆዬው አበበ ካሴም እንዲሁ በእስር ቤት በከፍተኛ ህመም እየተሰቃዬ እንደሚገኝ ታውቋል። በከፍተኛ የኩላሊት ህመም የሚሰቃየው አበበ፣ በደረሰበት ድብደባ ምክንያት ሽንቱን መቆጣጠር በማይችልበት ደረጃ ደርሷል። አበበ እንዲህ የተሰቃየሁበት ትግል ለውጡን ሳላይ እንዳልሞት መላው ኢትዮጵያውያን በየሃይማኖታችሁ በፀሎት አስቡኝ” ሲል ጥሪ አስተላልፏል።
ቃሊቲ የሚገኘው የህክምና ጣቢያ ከአቅሙ በላይ መሆኑን በመግለጽ ሌላ ቦታ ህክምና እንዲያገኝ ሪፈራል ቢጽፍለትም፣ እስር ቤቱ ውጭ ለማሳከም ፈቃደኛ አልሆነም። በአሁኑ ሰዓት በዝዋይ 65 በቃሊቲ ደግሞ ከ150 በላይ የፖለቲካ እስረኞች አሉ።
እንደ አበበ ሁሉ በተመሳሳይ ሁኔታ እጅግ አሰቃቂ ድብደባና ማሰቃያ የደረሰባቸው ዮናስ ጋሻውና አስቻለው ደሴ እንዲሁም ፓይለቶቹ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ፣ መቶ አለቃ አንተነህ ታደሰ፣ መቶ አለቃ ዳንኤል ግርማም እንዲሁ በእስር ላይ ናቸው።
በሌላ በኩል ደግሞ ተስፋዬ አያሌው በቅጽል ስሙ ሶራ የተባለው የአርበኞች ግንባር ታጋይ ፣ ሰኔ 4 ቀን 2010 ዓም በፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት 15 ዓመት ከ3 ወር እስር ፈርዶበታል። ተስፋዬ በጣም ጀግና ታጋይ ወጣት እንደሆነ የሚያውቁት ሰዎች ይናገራሉ። ኢትዮጵያ ውስጥ ከእነ አበራ ጎባው ጋር በመሆን ሲያስተባብር ቆይቶ በመታመሙ ሆስፒታል ውስጥ ተኝቶ መያዙን፣ ከተያዘም በሁዋላ መርማሪዎች በጻፉት ወረቀት ላይ ካልፈረመ ወንድሙን አስረው እንደሚያሰቃዩት ቢገልጹለትም ለረጅም ጊዜ በቃሉ ጸንቷል። ወንድሙ ተይዞ ማእከላዊ እስር ቤት ከገባና ስቃይ ከደረሰበት በሁዋላ፣ ወንድሙን ነጻ ለማውጣት ሲል እነሱ ባዘጋጁት ወረቀት ላይ መፈረሙን ወጣቱን በቅርብ የሚያውቁት ይናገራሉ። ከእርሱ ጋር በአንድ መዝገብ ውስጥ ከታሰሩት መካከል ክብር አለማየሁ፣ ጌታቸው ጋሻውና ደግ አረገ አይናለም ተፈትተዋል።