በሞያሌ የተሰወሩትን ወታደሮች ፍለጋ ቀጥሏል

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 13/2010)በሞያሌ ከትላንት በስቲያ የተሰወሩትን ወታደሮች ለመፈለግ የወጣው አሳሽ ቡዳን ዛሬም ፍለጋውን መቀጠሉ ተገለጸ።

ከ30በላይ ወታደሮች ከነሙሉ ትጥቃቸው ከተሰወሩ በኋላ በ10ኛው ክ/ጦር ባሉ ወታደሮች ዘንድ ውጥረት ነግሷል።

ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የሬዲዮ መገናኛ ኦፕሬተር መታሰሩን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

ወታደሮቹ ከተሰወሩ በኋላ በክ/ጦሩ የአማራና የኦሮሞ ተወላጅ በሆኑ የሰራዊቱ አባላት ላይ ጥብቅ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑንንም ለማወቅ ተችሏል።

ከትላንት በስቲያ ሰኞ ነው። በ10ኛ ክፍለጦር ውስጥ ከሚገኙ 3ሻለቃ መምሪያዎች በአንደኛው ያለ የጋንታ ሃይል ለመደበኛ ቅኝት ይወጣል።

ከ30 በላይ የሚሆኑ አባላት ያሉት የጋንታ አመራር ሙሉ ትጥቁን እንደያዘ ከሞያሌ ምድብ ቦታው ተነስቶ አካባቢውን ሊያስስ ሲወጣ የሚመለስበት ሰዓት የሚታወቅ ነበር።

ይሁንና በተባለው ሰዓት የጋንታው አመራር ወደ ካምፑ አልተመልሰም።

ግንኙነቱ ከማዘዣው ኮማንድ ሃይል ጋር መቋረጡ የታወቀው ትላንት በዕለቱ እንደነበርም ከኢሳት የመረጃ ምንጮች ለማወቅ ተችሏል።

ሌላ አሳሽ ግብረሃይል ተመድቦ ከትላንት ቀትር በኋላ ጀምሮ መላኩን የገለጹት የኢሳት ምንጮች እስከዛሬ ድረስ የጋንታው ሃይል እንዳልተገኘ ለማወቅ ተችሏል።

ከነሙሉ ትጥቁ የተሰወረው የጋንታ ሃይል የት እንደገባ ሳይታወቅ ሶስተኛ ቀኑን ይዟል።

በመከላከያው የህወሃት አዛዦች ዘንድ ከፍተኛ ድንጋጤን የፈጠረው የወታደሮቹ መሰወር በ10ኛ ክፍለጦር ውስጥ ውጥረት ማንገሱ የተገለጸ ሲሆን ዛሬ የ10አለቃ ረጋሳ የተባሉ የመገናኛ ኦፕሬተር መታሰራቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

የመገናኛ ኦፕሬተሩ የተሳሳተ መረጃ በማቀበል በሚል በክ/ጦሩ የህወሀት አዛዦች አማካኝነት የታሰረ ሲሆን ትክክለኛ ምክንያቱ ግን እንደማይታወቅ ምንጮች ገልጸዋል።

ወታደሮቹ የተሰወረበት ቦታና ምክንያታቸው ግራ ያጋባቸው የህወሃት አዛዦች በክ/ጦሩ ውስጥ የሚገኙት የአማራና የኦሮሞ ተወላጅ የሰራዊቱ አባላት ላይ ወታደራዊ ደህንነቶችን በመመደብ ጥብቅ ክትትል እንዲደረግ ማዘዛቸውም ተሰምቷል።

የተሰወሩት 30 ወታደሮች ናቸው ቢባልም ቁጥራቸው ከዚያ ሊበልጥ እንደሚችል የኢሳት ምንጮች ይገልጻሉ።

በ1ኛ ብርጌድ ውስጥ ካሉ 3 ሻለቃዎች ውስጥ ከነሙሉ የነፍስ ወከፍ ትጥቃቸው የተሰወሩት ወታደሮች አንድ የቡድን መሳሪያ እንደያዙና ቁጥራቸው ከ30 ሊበልጥ እንደሚችልም ነው የተገለጸው።

በወታደሩ ውስጥ ውጥረቱ የነገሰ ሲሆን የትግሬ አዛዦች ስብሰባ በተደጋጋሚ ሲያደርጉ ነበር።

የተሰወሩት ወታደሮች ታስቦበትና ታቅዶበት የተደረገ መክዳት ነው የሚለው አብላጫ ድምፅ ይያዝ እንጂ ታግተው ሊሆን ይችላል የሚል መላምትም ቀርቧል።

ነገር ግን ይሄን ያክል አባላት እንዴት ይታገታሉ? በማን? የሚለው ጥያቄ ተነስቶ እንደነበርና ምላሽ ለማግኘት እንደተቸገሩ ተገልጿል።

ትላንት የተሰወሩትን ወታደሮች ፍለጋ በሁለት ምዕራፍ የወጣው አሳሽና ፈላጊ ቡድኑ እስካሁን ወደ ቦታው ያልተመለሰ ሲሆን የአንድ ቀን ስንቅ ዛሬ እንደሄደላቸው ታውቋል።

ወታደሮቹ የተሰወሩበት ምክንያት ባይታወቅም በዚህ አካባቢ በህወሓት ቡድን በተቀሰቀሰው ዘር ተኮር ግጭት የብዙ ንፁሃን ሰዎች ህይወት ሲቀጠፍ በቦታው ያሉት ወታደሮች ከህወሓት ትግሬ አዛዦች ምንም አይነት ትዕዛዝ ባለመሰጠቱ ለማረጋጋትና በግጭቱ በመሃል ከመግባት እንዲቆጠቡ እንዳደረጋቸውና በዚህም ክፉኛ ያዘኑ ወታደሮች እንደነበሩ ታውቋል።

ከዚህ በፊትም በተደጋጋሚ ብዛት ያላቸው ወታደሮች በግዳጅ ላይ እያሉ እንደሚሰወሩ የተገለፀ ሲሆን ያሁኑ ግን በቁጥሩም በሁኔታውም ያልተጠበቀ መሆኑ በወታደሩ ዘንድ ከፍተኛ ውጥረትን አስከትሏል።

የወታደሮቹ መሰወርና መክዳት ያሳሰበው የህወሃት ቡድን ጥብቅ ቁጥጥር ለማድረግ የሚያስችል በወታደራዊ ደህንነት የሚመራ አንድ መዋቅር ማዘጋጀቱን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

በቅርቡ በብሄራዊ ደህንነት ምክርቤት በወጣ ዕቅድ የህወሀት መንግስት የጸጥታና የመከላከያ ሰራዊቱ እምነት እያጣበትና መንግስት ይቀጥላል ወይ የሚል ስጋት ውስጥ መግባቱን የሚገልጽበት ሰነድ ሾልኮ መውጣቱን መዘገባችን የሚታወስ ነው።