በሞያሌ ወታደሮችን የጫኑ ሁለት ኦራል መኪኖች በታጣቂዎች ተመተው ከተገለበጡ በሁዋላ በርካታ ወታደሮች አለቁ

በሞያሌ ወታደሮችን የጫኑ ሁለት ኦራል መኪኖች በታጣቂዎች ተመተው ከተገለበጡ በሁዋላ በርካታ ወታደሮች አለቁ
(ኢሳት ዜና ማጋቢት 07 ቀን 2010 ዓ/ም) ኦነግ የሞቱት ወታደሮች ቁጥር 72 ነው ይላል። የአካባቢው ነዋሪዎች ደግሞ የሟቾች ቁጥር 50 አካባቢ ነው ይላሉ።
ጥቃቱን ተከትሎም ኬንያ ድንበሯን ዘግታለች።
የኢሳት የአካባቢው ምንጮች እንደገለጹት 147 እና ወጀሌ በሚባለው አካባቢ አንድ ሙሉ ወታደሮችን የጫነ ኦራል መኪና በኦነግ ታጣቂዎች እንደተመታ ከሶስት ጊዜ በላይ ተገለባብጦ የወደቀ ሲሆን፣ መኪናው መገልበጡን ተከትሎ በወታደሮች ላይ የኦነግ ሃይሎች ጥቃት ከፍተው ብዙዎችን ገድለዋል። ይህንን ተከትሎ ከሁዋላ ሲጓዝ የነበረ ሌላ ኦራል መኪና የመጀመሪያው መኪና መገልበጡን ሲያይ ሹፌሩ በድንጋጤ መኪናውን የገለበጠው ሲሆን፣ በመኪናው ላይ የነበሩ ወታደሮች ብዙዎቹ አልቀዋል።
ኦነግ 72 ወታደሮች መገደላቸውን ሲገልጽ፣ የአካባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው እስከ 50 ወታደሮች ማለቃቸውን ተናግረዋል። ትናንት ምሽት ደግሞ 4 ሄሊኮፕተሮች በሞያሌ አካባቢ ሲያንዣብቡ መምሸታቸውን የአይን እማኞች ገልጸዋል። ሄሊኮፕተሮቹ ኬንያ ድንበር ዘልቀው በመግባት አሰሳ ሲያደርጉ ማምሸታቸውን ምንጮች አክለው ተናግረዋል።
ብሉምበርግ ዛሬ ይዞት በወጣው ዘገባ ደግሞ ኬንያ ከኢትዮጵያ ጋር የሚያዋስናትን ድንበር መዝጋቷን አስታውቋል። ኬንያ በእያንዳንዱ የድንበር መግቢያ ላይ 20 ሰዎችን የመደበች ሲሆን፣ 4 ታንኮችም በሁለት መግቢያ ቦታዎች ላይ ተመድበዋል።
በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ከሞያሌ የተሰደዱ ኢትዮጵያውያን ኬንያ ውስጥ በሶስት ቦታዎች ስፈረው ይገኛሉ። ለስደተኞቹ የሚሆን የምግብ እጥረት ከመከሰቱም በላይ፣ የንጹህ ውሃ አቅርቦትና ህክምና ባለመኖሩ አደጋ መደቀኑን የኬንያ ባለስልጣናት ተናግረዋል።