በሞያሌ ከተማ ዛሬም ግድያ አለመቆሙን የአካባቢው ነዋሪዎች ተናገሩ

በሞያሌ ከተማ ዛሬም ግድያ አለመቆሙን የአካባቢው ነዋሪዎች ተናገሩ
(ኢሳት ዜና ማጋቢት 03 ቀን 2010 ዓ/ም) ባለፈው ቅዳሜ በሞያሌ ከተማ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ከ13 ሰዎች በላይ መግደላቸውን ተከትሎ ግድያውና ውጥረቱ አሁንም ድረስ ያለ መሆኑን ነዋሪዎች ተናግረዋል። ትናንት ምሽት አንድ የኮንሶ ብሄረሰብ ተወላጅ ሌሊት ላይ በ10 ጥይቶች ተደብድቦ ተገድሎአል። አንድ የምዕራብ ጉጂ አካባቢ ተወላጅ የሆነ ወጣት ደግሞ በ 2 ጥይቶች ተመትቶ ቆስሏል።
ባለፈው ቅዳሜ የመከላከያ ሰራዊት ለፈጸሙት ጭፍጨፋ በህዝቡ፣ ወታደራዊ አዛዦችና የአገዛዙ ባለስልጣናት የተለያዩ ምክንያቶችን እየሰጡ ነው። የከተማዋ ነዋሪዎችና የአካባቢው ሰዎች ምንም ተቃውሞ ባልነበረበት ሁኔታ ወታደሮች እርምጃ መውሰዳቸው በግድያ በስልጣን ለመቆየት የሚደረግ ሙከራ እና ተስፋ የመቁረጥ ምልክት ነው ይላሉ።
የከተማዋ ከንቲባ አቶ አስቻለው ዮሃንስ “አካባቢው ላይ ምንም ዓይነት የፀጥታ ችግር አልነበረም ፤ ሕዝቡ በሰላማዊ እንቅስቃሴ ላይ ነበር። ልጁን አውርደው መቱት ከዛ በኋላ ወደ መንደሩ እያዞሩ መተኮስ ጀመሩ።” ሲሉ ለአሜሪካ ድምጽ ተናግረዋል።
ኮማንድ ፖስቱን በመወከል መግለጫ የሰጡት ሌ/ጄ ሃሰን ኢብራሂም ድርጊቱ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ኮማንድ ፖስት ጋር የተያያዘ ሳይሆን መደበኛ ወደ ኢትዮጵያ በመግባት ላይ የነበረውን የኦነግን ሰራዊት ለመከላከል በሚል በአካባቢው የተሰማራው አንድ ሻለቃ ጦር በተሳሳተ መረጃ የወሰደው እርምጃ ነው ብለዋል። ጄኔራሉ ድርጊቱ ከኮማንድ ፖስቱ ጋር እንደማይያያዝና የመከላከያ ጉዳይ ከሆነ የመከላከያ ተወካዮች መናገር ሲገባቸው እርሳቸው ለምን ኮማንድ ፖስቱን ወክለው መግለጫ እንደሰጡ ግልጽ አይደለም።
ሌሎች የመረጃ ምንጮች በበኩላቸው ከቅዳሜው እልቂት በፊት በሞያሌና 147 እየተባለ በሚጠራው ወታደራዊ ካምፕ አካባቢ ወይም ሚኦና ቱቃዩ በሚባሉ አካባቢዎች በመከላከያ ሰራዊት አባላት ላይ በደረሰ የቦንብ ጥቃት ከ6 ያላነሱ ወታደሮች መገደላቸውን ጠቅሰው፣ ጉዳት የደረሰባቸው የመከላከያ አባላት ሁሉም የትግራይ ብሄር ተወላጅ መሆናቸውንና የዚሁ ብሄር ተወላጅ የሆነው የሰራዊቱ አዛዥ ወታደሮቹ ወደ ከተማ ሄደው የበቀል እርምጃ እንዲወስዱ ማዘዙን ገልጸዋል።
ወታደሮቹ ወደ ሞያሌ በማቅናት ሸዋ በር በሚባለው አካባቢ በሚኖሩ ዜጎች ላይ የጅምላ ግድያ መፈጸማቸውን ምንጮች ተናግረዋል። የመከላከያ አዛዦች በስህተት የተወሰደ እርምጃ ነው በማለት ያቀረቡት ምክንያት ፍጹም ሃሰት ነው የሚሉት ምንጮች፣ በወታደሮቹ ላይ የቦንብ ጥቃቱን የፈጸሙት ሃይሎች እንደማይታወቁና ምናልባትም ከወታደሮች መካከል የተወሰኑት በአዛዦቻቸው ላይ ያቀናበሩት እርምጃ ሳይሆን እንደማይቀር ገልጸዋል።
ወታደራዊ አዛዡ በሰጠው የበቀል ትዕዛዝ መሰረት የተወሰኑ ወታደሮች ወደ ሸዋ በር በማምራት ለቅሶ ቤት፣ ሆቴል ውስጥ፣ ሱቅ ውስጥ እና መንገድ ላይ ያገኙትን ሁሉ መግደላቸውን ምንጮች ገልጸዋል። ጉዳት ከደረሰባቸው ሱቅ ከፍተው ሲጨጡ የነበሩ 2 የጉራጌ ተወላጆች፣ ምግብ በማስተናገድ ስራ ላይ የነበረ አንድ የወላይታ ተወላጅ፣ ለቅሶ ቤት ውስጥ ቁጭ ብሎ የነበረ አንድ ወጣት ይገኙበታል።
የበቀል እርምጃውን በመሸሽ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ወደ ኬንያ ተሰደዋል ። ለተፈናቀሉት ዜጎች ቀይ መስቀል አስፈላጊውን እርዳታ እያደረገላቸው እንደሆነ ታውቋል።
የመከላከያ ሰራዊት አባላት የወሰዱት እርምጃ ያስቆጣቸው የቡሌ ሆራ አካባቢ የሚኖሩ ወጣቶች መንገድ ላይ ዛፎችን እየቆረጡ በመጣል እስከ ዛሬ ረፋዱ ድረስ ተሽከርካሪ እንዳይሄድ አግደው ውለዋል።
በሌላ በኩል ዛሬ አድማ ይኖራል በሚል ፍርሃት ከሃረር ወደ አዲስ አበባ ይጓዝ የነበረው የአገር አቋራጭ የትራንስፖርት አግልግሎት ተቋርጦ መዋሉ ታውቋል። ኮሎኔል ተከስተ የተባለ ወታደራዊ አዛዥ የአገር አቋራጭ ሾፌሮችን ሰብስቦ የትራንስፖርት አገልግሎት ማቋረጥ እንደማይችልና በሚያቋርጡት ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ ቢገልጹም፣ የመኪኖቹ ባለቤቶች ግን፣ “መኪኖቹ መንገድ ላይ ቢቃጠሉ ኢንሹራንስ አይከፍለንም፤ እናንተ ውጡ ብላችሁ ታስገድዱናላችሁ፣ ጉዳቱ የሚደርሰው ግን እኛ ላይ ነው” በማለት ተቃውሞአቸውን ገልጸዋል።
ኮሎኔል ተከስተ ለተነሳው ተቃውሞ “መኪናችሁ ጉዳት ሲደርስበት እዛው ላይ አቁሙት፤ እርምጃውን በሚወስዱት ወጣቶች ላይ አስፈላጊውን እርምጃ እንወስዳለን፤ ጉዳቱ የደረሰበት ከተማ ነዋሪ የሆነው ህዝብ ካሳ እንዲከፍላችሁ እናደርጋለን” የሚል መልስ ቢሰጡም፣ ሹፌሮቹ ግን የማይሆን መልስ ነው በማለት ሳይቀበሉት ቀርተዋል።