በምዕራብ ወለጋ በሚገኙ የገጠር ቀበሌዎች የኦነግ ታጣቂዎች ከቄሮና አባገዳዎች ጋር በመሆን በማስተዳደር ላይ መሆናቸውን ነዋሪዎች ተናገሩ

በምዕራብ ወለጋ በሚገኙ የገጠር ቀበሌዎች የኦነግ ታጣቂዎች ከቄሮና አባገዳዎች ጋር በመሆን በማስተዳደር ላይ መሆናቸውን ነዋሪዎች ተናገሩ
( ኢሳት ዜና ጥቅምት 06 ቀን 2011 ዓ/ም ) ኦነግ በሰየ ወረዳ ወየ ቡቡካ በሚባለው ቀበሌ ከጥቅምት 1 ቀን 2011 ዓም ጀምሮ የመንግስት ታጣቂዎችን እንዲሁም በአካባቢው ከ32 ዓመታት ላላነሰ ጊዜ የሰፈሩትን የአማራ ተወላጆች መንግስት ፈቅዶላቸው የያዙትን የነፍስ ወከፍ የጦር መሳሪያ፣ የወያኔ ታጣቀዊዎች ናችሁ በማለት ትጥቅ እያስፈታ መውሰዱን ነዋሪዎች ተናግረዋል። የኦነግን ጥቃት በመፍራት ጫካ የገቡ ሰዎች መኖራቸውንም ነዋሪዎች ገልጸዋል።
አካባቢውን የኦነግ ታጣቂዎች፣ ቄሮዎችና አባ ገዳዎች በጋራ ተመራርጠው እያስተዳደሩት ሲሆን፣ የመንግስት አካላት በአካባቢው አለመኖራቸውን ተናግረዋል። መንግስት እርምጃ እንዲወስድ ለኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት ቢያመለክቱም ጠብቁ የሚል መልስ ከማግኘት የዘለለ ምላሽ እንዳላገኙ ነዋሪዎች ገልጸዋል። በጉዳዩ ዙሪያ የመንግስት ባለስልጣናትን መልስ ለማግኘት ያደረግነው ጥረት አልተሳካም።