በምስራቅ ሀረርጌ በተለያዩ ከተሞች በተነሳ ተቃውሞ 6 ሰዎች ተገደሉ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 20/2010)በምስራቅ ሀረርጌ በተለያዩ ከተሞች በተነሳ ተቃውሞ 6 ሰዎች ተገደሉ።

በአዳማ ናዝሬት ዛሬ በተቀሰቀሰው ግጭት 2 ነዋሪዎች በአጋዚ ሰራዊት መገደላቸው ታወቋል።

በምስራቅ ሀረርጌ ጨለንቆ፣ ጉርሱም፣ በደኖና ባቢሌ ህዝባዊ አመጽ ተነስቶ ከመንግስት ታጣቂዎች ጋር ግጭት መፈጠሩንም የደረሰን ዜና ያመለክታል።

በአምቦ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ግቢውን ለቀው እየወጡ ነው። በተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች ውጥረቱ ተባብሶ መቀጠሉም ታውቋል።

የህወሃት ደህንነቶች በኦነግ ስም ወጣቶችን እየመለመሉ በማሰር ላይ መሆናቸውን ለኢሳት የደረሰው መረጃ አመልክቷል።

ዛሬ በተለያዩ የኦሮሚያ ክልል አካባቢዎች በትንሹ ስምንት ሰዎች ተገድለዋል።

የሶማሌና የኦሮሚያ ክልል ግጭት ዳግም ባገረሸበት በዚህ ሰሞን ምስራቅ ሀረርጌ በህዝባዊ ተቃውሞ እየተናጠች ነው።

በግጭቱ የተፈናቀሉትን ለመርዳት የተንቀሳቀሰው ህዝብ ላይ የመከላከያ ሰራዊትና የሶማሌ ክልል ልዩ ሃይል ርምጃ በመውሰድ ከ6 በላይ ሰዎችን መግደላቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

ካለፈው ሰኞ ጀምሮ በጨለንቆ፣ በጉርሱም፣በበደኖ፣ በባቢሌ፣ በአወዳይና በሌሎች ከተሞች ህዝባዊ ንቅናቄ የተቀጣጠለ ሲሆን የመከላከያ ሰራዊት በቀጥታ ተሳታፊ ሆኖ ርምጃ በመውሰድ ላይ ነው።

ዛሬ በአዳማ በተከሰተው ግጭት ሁለት ሰዎች መገደላቸውንም ከአካባቢው የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

ህገወጥ መኖሪያ ቤቶች ገንብታችኋል በሚል ለማፍርስ ከመጣ ግብረሃይል ጋር ግጭት የተፈጠረ ሲሆን ነዋሪው ላይ የአጋዚ ሰራዊት ፊት ለፊት መተኮሱም ታውቋል።

በቁጣ ላይ የነበረው የአዳማ ነዋሪ ወደ አሰላ የሚወስደውን ዋና መንገድ በድንጋይ በመዝጋት ለረጅም ሰዓታት እንቅስቃሴ እንዲቆም ማድረጉ ተገልጿል።

በዚህን ወቅት በ2 ኦራል ወታደራዊ ተሽከርካሪዎች ስኳር ተጭኖ ያገኘው ነዋሪ በሃይል በማስቆም ስኳሩን መከፋፈሉን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

በአዳማ የተነሳው ተቃውሞ እስከ አሰላ መዝለቁንም የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

በተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የተጀመረው ተቃውሞ ቀጥሎ ዛሬ ከአምቦ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ግቢውን ለቀው በመውጣት ላይ መሆናቸውንም ለማወቅ ተችሏል።

በኢሉባቡር ያዩ በህገወጥ መንገድ የከሰል ምርት እያወጣ የሚሸጠውንና የህወሀት ጄነራሎች የሚመሩት ሜቴክ ድርጅት ላይ ተቃውሞ የተነሳ ሲሆን በደሌ ላይ ከሰል የጫነ የሜቴክ ተሽከርካሪ በቄሮዎች መታገቱን ከደረሰን መረጃ ለማወቅ ተችሏል።

በሌላ በኩል የህወሃት ደህንነቶች በኢሉባቡር አካባቢ ወጥረቶችን በኦነግ ስም እያታለሉ በመመልመል ለእስር እየዳረጓቸው መሆኑ ታውቋል። የኦነግ አባላት ነን።

በድብቅ ጫካ ውስጥ ታጣቂዎቻችን ስልጠና ላይ ናቸው እያሉ የሚቀርቡት የደህንነት ሰዎች ወጣቶችን መልምለው ከወሰዱ በኋላ እስር ቤት አስገብተው ሌሎች ወጣቶችን እንዲጠቁሙ በማድረግ ላይ ናቸው ተብሏል።