በመከላከያ አዛዦች የሚመራው ሜቴክ አገሪቱን ለከፍተኛ እዳ እየዘፈቃት ነው ተባለ

ግንቦት ፫(ሦስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በህወሃቱ ጄኔራል ክንፈ ዳኘው የሚመራውና በአንድ ወቅት አቶ መለስ ዜናዊ “የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ እድገት አቅጣጫ የሚቀይስ ተቋም” ብለው ያሞካሹት በመከላከያ ስር የሚገኘው የብረታብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ( ሜቴክ) በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገነቡ ፕሮጀክቶች መጓተት እንዲሁም በማህበራዊ አገልግሎት ዘርፍ ለሚታዩ ችግሮች ዋና ተጠያቂ መሆኑን የመንግስት ባለስልጣናት መናገር ጀምረዋል። ይሁን እንጅ የሜቴክ አመራሮችን ደፍሮ የሚጠይቃቸው በመጥፋቱ፣ አገሪቱ ዋጋ እንድትከፍል እየተደረገ ነው።
የውሀ፣ መስኖና አሌክትሪክ ሚኒስቴር ምንጮች እንደጠቆሙት ከውጭ ምንዛሪ እጥረት ጋር በተያያዘ የኤሌክትሪክ ሀይል አፈጻጸሙ በአስደንጋጭ ሁኔታ ያሽቆለቆለ ሲሆን፣ በያዝነው የኢትዮጵያ 2008 በጀት አመት ስምንት ወራት ለ390 ሺ ደንበኞች አዲስ የኤሌክትሪክ ሀይል ለማገናኘት ታቅዶ ማሳካት የተቻለው 78 ሺ 254 ወይንም የእቅዱን 20 በመቶ ብቻ መሆኑ ሲሆን፣ አፈጻጸሙ ሊያሽቆለቁል የቻለው ከውጭ ሀገር ተገዝተው መግባት ያለባቸው እቃዎች በውጭ ምንዛሪ ችግር ምክንያት በወቅቱ ሊገዙ ባለመቻላቸው እንዲሁም፣ የብረታብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን በሀገር ውስጥ አምርቶ ማቅረብ የነበረበትን በወቅቱ ማቅረብ ባለመቻሉ ነው።
በሀገር አቀፍ ደረጃ የኤሌክትሪክ አቅርቦት ፕሮግራም አማካኝነት ለ572 የገጠር ከተሞች እስከ የካቲት 30 የሀይል ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ መፈጸም የተቻለው 256 ቀበሌዎችን ወይንም የእቅዱን 45 በመቶ ብቻ ነው።
የኤሌክትሪክ ሀይል አገልግሎት መ/ቤት አፈጻጸም ከራሱ እቅድ ጋር ያሳየው የአፈጻጸም ድክመት ከዚህ ቀደም ታይቶ የማይታወቅ ሲሆን ከውጭ ምንዛሪ ችግሩ በተጨማሪ ሜቴክ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ እያሽመደመደ መሆኑን ምንጮች ይገልጻሉ።
ሜቴክ ከስኳር ግንባታ ጋር በተያያዘም አገሪቱን ለከፍተኛ እዳ እየደረጋት መሆኑንና የስኳር ኮርፖሬሽን ስራ አስኪያጅ ሜቴክን ደፍሮ የሚናገረው አካል ባለመኖሩ አገሪቱ ችግር ውስጥ እየገባች መሆኑን ተናግረዋል።
ሪፖርተር የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን የሥራ ኃላፊዎች በ2008 የበጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ግንቦት 1 ቀን 2008 ዓ.ም ያቀረቡትን በመንተራስ በሰራው ዘገባ ላይ ሜቴክ በአገሪቱ ላይ እያደረሰ ያለውን ጉዳት በዝርዝር ዘግቧል።
77 ቢሊዮን ብር የተመደበላቸው 10 የስኳር ፕሮጀክቶች አምና ስራ ሲጀምሩ 1 ቢሊዮን 200 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ያስገኛሉ ተብሎ ሲጠበቅ፣ ከአስሩ አንዳቸውም ስራ መጀመር ያልቻሉ ሲሆን አገሪቱ ግን ከውጭ ባንኮች ለተበደረችው 2 ቢሊዮን ዶላር ወለድ 13 ቢሊዮን ብር እዳ መክፈል ትጀምራለች።
አንድ የስኳር ፋብሪካን ለማጠናቀቅ ግፋ ቢል አንድ ዓመት የሚፈጅ ቢሆንም፣ የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ኮርፖሬሽን ግን በአንድ አመት ከመንፈቅ ለማጠናቀቅ እቅድ ይዞ፣ አንዳቸውም ስራ ሳይጀምሩ ስድስተኛ ዓመታቸውን ይዘዋል። የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ እንዳወቅ አብቴና ሌሎች ምክትል ሥራ አስፈጻሚዎች ‹‹ተስፋ እየቆረጥንና እያመመን ነው›› ሲሉ ለፓርላማ ተወካዮች ተናግረዋል።
ተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ ከ7 አመታት መጓተት በሁዋላ በኅዳር ወር 2008 ዓ.ም. ስኳር ማምረት ቢጀምርም ጥራቱ የተጓደለ የእንፋሎት አቅርቦት፣ የፋብሪካውን ፊልተር በቆሻሻ በመዝጋቱና በተርባይን ላይ ጉዳት በማድረሱ እንዲቆም የተደረገ ሲሆን፣ ጥገና ከተደረገ በኋላም ቢሆን በአገሪቱ በተከሰተው ድርቅ ለፋብሪካውና ለመስኖ የሚሆን የውኃ አቅርቦት ችግር ወደ ምርት እንዳይገባ አድርጎታል።
የተንዳሆ ቁጥር ሁለት ፋብሪካ ግንባታም ገና 27 በመቶ ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ ኩራዝ አንድ የተባለው ፋብሪካ ውሉ በ2003 ዓ.ም ተገብቶ ከሁለት አመት በፊት ተጠናቆ ስራ መጀመር የነበረበት ቢሆንም ፕሮጀክቶ ገና አልተገባደደም።
ለዚህ መጓተት ዋናው ተጠያቄ ደግሞ የመከላከያ ኢንጂነሪንጉ ሜቴክ ነው። ድርጀቱ 97 በመቶ የሚሆን ክፍያ የተፈጸመለት ቢሆንም፣ ፕሮጀክቱን መቼ አጠናቆ እንደሚያስረክብ አይታወቅም።
ኩራዝ አምስት ስኳር ፋብሪካን ለማስጀመር ከቻይና ኩባንያ ጋር ውል የተፈጸመ ቢሆንም፣ ወደ ሥራ ለመግባት ኩባንያው ዝግጅት ላይ መሆኑን አቶ እንዳወቅ ገልጸዋል፡ በለስ አንድ ስኳር ፕሮጀክት ወደ ሥራ የገባው በየካቲት 2003 ዓ.ም ነው ሲሆን የፕሮጀክቱ አፈጻጸም በአሁኑ ወቅት ገና 60 በመቶ ላይ ሲሆን፣ ሜቴክ ግን 94 በመቶ የሚሆነውን ክፍያ ተቀብሎአል።
በለስ ሦስት ፋብሪካን በ2 አመታት ውስጥ ተገንብቶ በ2005 መጋቢት ላይ ወደ ስራ መግባት የነበረበት ቢሆንም፣ ፕሮጀክቱ ገና 23 በመቶ ላይ የቆመ ሲሆን፣ ኮንትራክተሩ ሜቴክ 94 በመቶ ክፍያ ወስዷል። የከሰም ስኳር ፋብሪካ አፈጻጸም 96 በመቶ ቢደርስም ገና ወደ ስራ አልገባም፤ የወልቃይት ስኳር ፋብሪካም ግንባታው አልተጀመረም።
የአሥሩም አዳዲስ ፋብሪካዎች ኮንትራት የተሰጠው ለ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ቢሆንም፣ ኮርፖሬሽኑ ግን ፋብሪካዎቹን መገንባት እንዳልቻለ ተናግረው፣ የቀድሞዎቹ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን አመራሮች ከሜቴክ ጋር የነበራቸው ግንኙነት በቢዝነስ ኮንትራት ሕግ የማይመራ ባለመሆኑ ድርጅቱን ተጠያቂ ለማድረግ አለመቻሉን ይገልጻሉ።
4 ቱ ድርጅቶች ከሜቴክ ተወስደው ለሌሎች ከተሰጡ በሁዋላ ስራቸው ቢጀመርም፣ በሜቴክ እጅ የሚገኙት ግን መቼ እንደሚጠናቀቁ እንኳን ለማወቅ አስቸጋሪ እንደሆነባቸውና ከድርጅቱ ጋር ልቅ የሆነው ግንኙነት በውል ያልታሰረ በመሆኑ ዕርምጃ እንኳን ለመውሰድ እንዳልተቻለ ተናግረዋል፡፡
ሜቴክ በእጁ የሚገኙትን ሦስት ፋብሪካዎች በተለይም ኩራዝ አንድ ፋብሪካን በመጋቢት ወር 2007 ዓ.ም ለማጠናቀቅ ገንዘብ እንደሚያስፈልገው ገልጾ፣ በልዩ ሁኔታ በሚል ስኳር ኮርፖሬሽን የአገር ውስጥ ብድር እንዲያገኝ ተደርጎ ቢከፈለውም ፋብሪካው እስካሁን አለመጠናቀቁን የገለጹት ሃላፊዎች፣ ዕዳ የመክፈል አደጋ ከፊታችን ተጋርጧል ሲሉ ምሬታቸውን ገልጸዋል።
ፋብሪካዎቹ ባለመድረሳቸው ምክንያት አጠቃላይ የስኳር ኮርፖሬሽን ወጪ እየናረ መሆኑን የሚገልጹት የሥራ ሃላፊዎች፣ ፋብሪካዎቹ ባለመድረሳቸው ምክንያት ኩራዝ ላይ 870 ሔክታር አገዳ ሊወገድ ሲሆን፣ በለስ ላይ ደግሞ 300 ሺሕ ሔክታር የሸንኮራ አገዳ ተወግዷል የሚሉት ባለስልጣናቱ፣ የማስወገዱን ስራ ለመስራት በሔክታር 50 ሺሕ ብር መውጣቱንም ገልጸዋል።
ባለስልጣናቱ በሜቴክ ላይ እንደ ማንኛውም ኩባንያ ቅጣት መጣል እንደማንችል ሁላችሁም ታውቃላችሁ፡፡ የሚያስጠይቅ ነገር ካለ ባለቤቱ ተለይቶ መጠየቅ ያስፈልጋል በማለት የሜቴክ ወታደራዊ አመራሮች ከህግ በላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። በማምረት ላይ ለሚገኙ ፋብሪካዎች መለዋወጫ የሚያቀርበው ሜቴክ ፣ መለዋወጫ ባለማቅረቡ ምክንያት ፋብሪካዎች ለበርካታ ቀናት ምርት እንደማያመርቱም አጋልጠዋል፡፡
‹‹የማይችሉትን ሁሉ እንችላለን እያሉ አገርን ዋጋ እያስከፈሉ ነው፡፡ ምክንያቱም ነባሮቹ ፋብሪካዎች ያለምንም ችግር ቢሠሩ ኖሮ ወደ ውጭ መላካችን ቀርቶ ቢያንስ የውጭ ምንዛሪ እያወጣን ስኳር አናስገባም ነበር፤›› የሚሉት ሃለፊዎቹ፣ መለዋወጫ ከሜቴክ የመግዛት ግዴታ ለአገሪቱ አዋጭ አለመሆኑን፣ ሜቴክ ከውጭ ከሚገባው በላይ በሆነ ዋጋ እየሸጠ መሆኑን ገልጸዋል።
የስኳር ኮርፖሬሽኑ ሃላፊዎች ‹‹እንቢ ብለን እንኳን እንዳንታገል አመራሮች ያሸማቅቁናል›› ሲሉ ችግሩ ከአቅማቸው በላይ መሆኑን ተናግረዋል። የስኳር ድርጅቶቹን በበላይነት ሲመሩ ከነበሩት ባለስልጣናት መካከል አቶ አባይ ጸሃዬ አንዱ ናቸው።
ሜቴክ በአባይ ግድብ ዙሪያም ድርሻ ወስዶ እየሰራ መሆኑ ይታወቃል። ሜቴክ የሚወስዳቸውን ስራዎች ከማጓተቱም በላይ ጥራት አልባ በመሆናቸው አገሪቱን ለከፍተኛ እዳ እና ችግር እየዳረጋት መሆኑን ኢሳት በተደጋጋሚ ሲዘግብ ቆይቷል። በሙስና የተዘፈቁት የህወሃት ጀኔራሎች፣ ከሜቴክ ከሚዘርፉት ገንዘብ በተጨማሪ፣ በሜቴክ ስም ከቀረጥ ነጻ የሆኑ እቃዎችን በማስገባት የአገሪቱን የእቃዎች ንግድ ይቆጣጠራሉ።
ሜቴክ በአጼ ሃይለስላሴና በደርግ ዘመን የተገነቡ ፋብሪካዎችን በመውሰድ የተቋቋመ ኩባንያ ሲሆን፣ ህወሃት በመንግስት ስር አድርጎ ያቋቋመው የዝርፊያ ተቋሙ ነው በማለት ሰራተኞች በተደጋጋሚ ሲናገሩ ይሰማል። በስሩ የሚገኙት ኩባንያዎች በአብዛኛው በአንድ አካባቢ ሰዎች የሚመራ ሲሆን፣ ሰራተኞቹ ኢፈርት የተባለውን የህወሃት ግዙፍ ኩባንያ እና ሜቴክን ለይቶ ማዬት እንደማይቻል ይናገራሉ።