በለውጡ ሂደት እጁን መሰብሰብ ያለበት ሃይል እጁን እንዲሰበስብ ይደረጋል ተባለ

      (ኢሳት ዲሲ– ሰኔ 26/2010)በለውጡ ሂደት እጁን መሰብሰብ ያለበት ሃይል እጁን እንዲሰበስብ ይደረጋል ሲሉ በአውስትራሊያ የኢትዮያ አምባሰደር ገለጹ።

የህወሀት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል የሆኑት አምባሳደር ትርፉ ኪዳነማርያም ኤስ ቢ ኤስ ለተሰኘ ሬዲዮ ጣቢያ በሰጡት ቃለ መጠይቅ ላይ እንደገለጹት፡ የትግራይ ህዝብ እየተናገረ ነው። ለውጥ ያስፈልጋል። ህወሀት ውስጥም ለውጥ መደረግ አለበት ብለዋል።

ህወህት እየታየ ያለውን ለውጥ ተገንዝቦ በድርጅቱ ውስጥ ተመሳሳይ ለውጥ እንዲኖር ያደርጋል ብዬ እጠብቃለሁ ያሉት አምባሳደር ትርፉ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የተጀመረው የለውጥ ሂደት ከውጤት እንደሚበቃ እተማመናለሁ ሲሉ ገልጸዋል።

የቀድሞ የኢንሳ ዳይሬክተር ሜጀር ጄነራል ተክለብርሃን ወልደአረጋይ ሰሞኑን ለድምጸ ወያኔ በሰጡት ቃለመጠይቅ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይን አስተዳደር የጠላት ሃይል ሲሉ መፈረጃቸው የሚታወስ ነው።