በሃረሪ ፖሊስ ኮሚሽን መሳሪያ ግምጃ ቤት ውስጥ የበርካታ ሰዎች አጽም ተገኘ

በሃረሪ ፖሊስ ኮሚሽን መሳሪያ ግምጃ ቤት ውስጥ የበርካታ ሰዎች አጽም ተገኘ
( ኢሳት ዜና ሃምሌ 10 ቀን 2010 ዓ/ም ) ዛሬ ሃምሌ 10 ቀን 2010 ዓም በፖሊስ ኮሚሽን ግቢ ውስጥ በጓሮ በኩል የወዳዳቁ የሰው አጽሞች የተገኙ ሲሆን፣ እንዲሁም አሰሳ ያደረጉት ቄሮዎች እዛው አካባቢ ሌላ በጆንያ የተጠቀለለ ሌላ አጽም አግኝቷል። አዲሱ የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ኦድሪን በድሪና ምክትሉ አቶ ነቢል መሃዲ እንዲሁም የኦህዴድ ተወካይ የሆኑት የሃረሪ ክልል ፍትህና ጸጥታ ሃለፊ አቶ አበበም በስፍራው ተገኝተዋል።
አቶ አበበ ከፖሊሶች ባገኙት ጥቆማ መሰረት መሳሪያ ግምጃ ቤቱም እንዲከፈት ያስደረጉ ሲሆን፣ የመሳሪያ ግምጃ ቤቱ ሃላፊ ወ/ሮ አበበች የተባሉ ግለሰብም “ ኮሚሽነር አብዱልፈታህ አብድልቃድር በነበሩ ጊዜ በማዳበሪያ ቋጥረው አንድ የማላውቀው ነገር ይቀመጥ ብለው በአንድ ክፍል ውስጥ ማስገባታቸውንና እኔም ሽታው አላስቀምጠኝ አለ፣ ለአስም በሽታም ተደረኩ” ብዬ ባመለክትም ዝም በይ መባላቸውን ገልጸዋል። አሁን ላሉት ኮሚሽነር ነስሩ አሊምም አመልክተውም “ዝም በይ ተይው” መባላቸውን ተናግረዋል። የፍትህና ጸጥታ ሃላፊው ከፖሊሶች ጋር ሆነው ግምጃ ቤቱ ሲከፈት አፉ በጨርቅ የታሰረ የሰው አጽም በጨርቅ ተጠቅልሎ አግኘተዋል።
ወኪላችን እንደገለጸው ሁለት ጆንያ አጽም መሰብሰቡንና የሃረሪ ክልል የወንጀል መከላከል ኮሚሽነር ጀማል፣ የመስራቅ ሃረርጌ ም/ል አስተዳዳሪ፣ የኮሚኒኬሽን እና የኦፒዲዮ ሃላፊዎች ተሰብስበው ከቄሮች ጋር ተሰብስበው፣ አጽሙ ከየት እንደመጣ፣ ግምጃ ቤት ውስጥ ያስገባው ማነው የሚለውን ለማወቅ ከቄሮዎችና ከፖሊሶች የተውጣጡ ሰዎች ምርምራ እንዲያካሂዱ ተወክለዋል።
የሃረሪ ክልል ፖሊስ ሃላፊነት ወስዶ አጽሙ በአንድ ክፍል ውስጥ እንዲገባ መደረጉን ወኪላችን ዘግቧል።