ስዋዚላንድ ስሟ ተቀየረ

(ኢሳት ዲሲ–ሚያዚያ 12/2010)  የስዋዚላንዱ ንጉስ የሃገራቸውን ስያሜ መቀየራቸው ተሰማ።

ንጉስ ምስዋቲ  የሃገራቸውን ስያሜ መቀየራቸው በብዙዎች ዘንድ ያለተለመደ ነው ብሎታል ቢቢሲ በዘገባው።

የስዋዚላንድ ዜጎችም ከስም ለውጥ ይልቅ በኮኖሚ ጉዳዮች ላይ ቢያተኩሩ  ይሻላል ሲሉ ርምጃውን ተቃውመዋል።ስዋዚላንድ አዲሱ  መጠሪያዋ ኢስዋትኒ መሆኑም ታውቋል።

ሳልሳዊ ንጉስ ምስዋቲ ሃገራቸው ስሟ መቀየሩን ያወጁት የስዋዚላንድ 50ኛ አመት የነጻነት በአል በተከበረበት ስነስርዓት ላይ ነው።ስዋዚላንድ ከዚህ በኋላ የምትጠራበት ስያሜም ኢስዋትኒ ሆኗል ብለዋል ንጉሱ። ኢስዋትኒ ማለት ደግሞ የስዋትኒዎች ምድር እንደ ማለት ነው ብሏል ዘገባው።

እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2014 የተባበሩት መንግስታት ስብሰባ ላይ ንጉሱ ሀገራቸውን ኢስዋዚ በማለት ሲጠሩ ተሰምተዋል።

እናም ይህን ግርታ ለማጥራት በሚል ስያሜውን መቀየራቸውን ነው ያስታወቁት። ንጉስ ምስዋቲ በሃገራቸው ፈላጭ ቆራጭ የሚባል ስርአትን ያራምዳሉ በሚልም ስማቸው ይነሳል።

ሀገራቸው ከቅኝ ግዛት ነጻ ከወጣች 50 አመታትን አስቆጥራለች።ሃገሪቱ ነጻነቷን ካወጀችበት ጊዜ አንስቶም በንጉሳዊ ቤተሰብ ስር ቆይታለች።

አሁን ያሉት ንጉስ ሳልሳዊ ምስዋቲ ለ 32 ዓመታት በስልጣን ላይ ቆይተዋል።

ሀገሪቱ በየአመቱ የምታከብረው የነጻነት በአልም እንደ ንጉሱ የልደት ቀን ተደርጎ ይቆጠራል ብሏል ዘገባው።

በሰብአዊ መብት ጥሰትና በተለይም ሴቶችን በማግለል የሚታወቀው አስተዳደራቸው ከስም መቀየር ይልቅ ትኩረቱን ሌሎች ነገሮች ላይ ቢያደርግ የሚሉ ጥያቄዎች መነሳታቸውንም ዘገባው አመልክቷል።