ሱልጣን ሃንፍሬ አሊሚራህ ከስደት ተመለሱ

(ኢሳት ዲሲ–ነሐሴ 8/2010)  የአፋር መንፈሳዊ መሪ ሱልጣን ሃንፍሬ አሊሚራህ ከስደት ተመለሱ።በከሱልጣን ሃንፍሬ አሊሚራህ ጋር የአፋር ሕዝብ ፓርቲ መሪ ዶ/ር  ኮንቴ ሙሳ እንዲሁም የአፋር ሰብዓዊ መብት ድርጅት ሊቀመንበር አቶ ጋአስ አህመድም  በተመሳሳይ ኢትዮጵያ ገብተዋል።

በተመሳሳይ ዜና የኦሮሞ ነጻነት ግንባር አመራሮችም ዛሬ  ወደ  ኢትዮጵያ ተመልሰዋል።

ከአምስት አመታት በፊት የሱልጣን አሊ ሚራህን ማለፍ ተከትሎ፣ የሱልጣን ማዕረጉን የወረሱትና ባዕለ-ሲመታቸውን በአፋር ክልል በአሳይታ   ከተማ  ያካሄዱት ሱልጣን ሃንፍሬ አሊሚራህ  ሥልጣን ላይ ካለው መንግስት ጋር ባለመስማማት እና  በሕዝብ ላይ የሚደርሰወን በደል በመቃውም ከሃገራቸው ከተሰደዱ ጥቂት ኦመታትን አስቆጥረዋል።

በውጭ ሃገር ቆይታቸው ለአፋር ሕዝብ በጥቅል ለኢትዮጵያውያን መብት ሲታገሉ  መቆየታችው የተገለጸው  ሱልጣ ሃንፍሬ አሊሚራህ እና በርሳቸው የተመራው ልኡክ ዛሬ   አዲስ አበባ ሲደርስ የፌደራል እና የአፋር ክልል ባለሥልጣናት አቀባበል አድርገውላቸዋል።

ሱልጣን ሃንፍሬ አሊሚራህ ከአምስት ዓመት በፊት  በአሳይታ በዓለ ሲመታቸውን ሲያከብሩ  የጅቡቲውን ጠቅላይ ሚኒስቴር ጨምሮ 11 ሚኒስትሮች እንዲሁም በሺዎች የሚቆጠሩ አፋሮች ከኤርትራና ከጅቡቲ በክብረ-በዓሉ ሲገኙ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት አለመሳተፋቸውን ሱልጣን ሃንፍሬ አሊሚራህ ለኢሳት መግለጻቸው ይታወሳል።

የኢትዮጵያ ባለስልጣናት በበዓለ ሲመቱ ላይ አለመገኘት ብቻ ሳይሆን  ኢትዮጵያውያን አፋሮች እንዳይገኙ የተለያዩ ተፅዕኖ ማድረጋቸውን እንዲሁም ሂደቱን ለማደናቀፍ 2 ሚሊዮን ብር መመደባቸውንም ከዓመት በፊት ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ በዝርዝር ተመልክተዋል።

አፋሮች  በሁሉም መስክ ግፍ እና በድል ሲፈጸምባችው መቆየቱን  እንዲሁም ከፍተኛ የሃብት ምዝበራ መካሄዱንም መግለጻቸው አይዘነጋም።

ይህ በእንዲህ እንዳለም ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ባለፈወ ሳምንት የሰላም ስምምነት የተፈራረመው የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ልኡካን ዛሬ አዲስ አበባ ገብተዋል።  የግንባሩ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል እና ቃል አቀባይ በሆኑት  በአቶ ቶሌራ አዳባ የተመራው ልኡክ አዲስ አበባ ሲገባ የኦህዴድ እና የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት አቀባበል አድረገውለታል።

የግንባሩ ሊቀመንበር አቶ ዳውድ ኢብሳ በቀርቡ ወደ ሃገራቸው ይመለሳሉ ተብሎም ይጠበቃል።

የኦጋዴን ብሄራዊ ነጻነት ግንባር ልኡካን ቅዳሜ አዲስ አበባ መግባታቸው ይታወቃል ።

የአርበኞች ግንቦት 7 አመራሮችን የጨመረው የአርበኞች ግንቦት  ቡድን በቅረቡ አዲስ አበባ እንድሚገባም ከወጣው መርሃ ግብር መረዳት ተችሏል።