ራይላ ኦዲንጋ ኬንያን ወክለው በዊኒ ማንዴላ የቀብር ስነ ስርአት ላይ ተገኙ

(ኢሳት ዲሲ–ሚያዚያ 8/2010) የኬንያው የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ራይላ ኦዲንጋ ኬንያን ወክለው በዊኒ ማንዴላ የቀብር ስነ ስርአት ላይ መገኘታቸው ተሰማ።

ራይላ ኦዲንጋ በቀብር ስነስርአቱ ላይ የተገኙት በሃገሪቱ መንግስት ተወክለው መሆኑንም ቢሮአቸው አስታውቋል።

የራይላ ኦዲንጋ ወደ ስፍራው መጓዛ በሀገሪቱ የተፈጠረው ሰላምን የማውረድ ሒደት ውጤታማ መሆኑን ማሳያ ነው ተብሏል።

በመጨባበጥ የተጀመረው የኡሁሩ ኬንያታና የተቃዋሚ ፓርቲ መሪው ራይላ ኦዲንጋ ቅርርብ በርካቶችን አስገርሞ ነበር።

አሁን ላይ ግን የተቃዋሚ ፓርቲ መሪው ራይላ ኦዲንጋ ሀገራቸውን ወክለው በነጻነት ታጋይዋ ዊኒ ማንዲላ የቀብር ስነስርአት ላይ እንዲገኙ ተደርገዋል ይላሉ ከአካባቢው የወጡ መረጃዎች።

የአሁኑን ሒደትም በርካቶች በበጎ አይን ማየታቸውን ዘገባዎቹ አመልክተዋል።