ሙስሊም ኢትዮጵያውያን በአንዋር መስጊድ ሰላማዊ ተቃውሞዎችን ቀጥለው ዋሉ

ሐምሌ ፳፯ (ሀያ ስድስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በአዲስ አበባ እና በአዲስ አበባ ዙሪያ ባሉ ከተሞች የሚኖሩ ሙስሊም ማህበረሰብ ዛሬ ከቀኑ 5 ሰአት ተኩል ጀምሮ በአንዋር መስጊድ በመሰባሰብ የአርብ ስገደት ካደረጉ በሁዋላ ፣ ሰላማዊ ተቃውሞዎችን ቀጥለው ውለዋል።

ቁጥራቸው ከ5 መቶ ሺ በላይ ሙስሊሞች ፣ የሚወርደው ዶፍ ዝናብ ሳይበግራቸው ፣ ከጸሎት በሁዋላ ለደቂቃዎች ነጭ ማህረብ ጨርቅ ፣ ነጭ ሶፍት ወረቀት በማውለብለብ፣ ሰላማዊነታቸውን ያሳዩ ሲሆን ፣ እጅ ለእጅ በመያያዝ አንድነታቸውን ገልጸዋል። አፋቸውን በጨርቅ በማሸግ፣  እጃቸውን በካቴና እንደታሰሩ በማስመሰል የመንግስት ፌደራል ፖሊስ ያደረሰባቸውን ድብደባ፣ እስርና አፈና በምልክት ገልጸዋል። ተንበርክከው እጃቸውን ወደ ላይ በመዘርጋት በፈጣሪያቸው እንደሚተማመኑ የሚመኩትም በፈጣሪያቸው መሆኑን አሳይተዋል ይላል ዘጋቢያችን።

ዘጋቢያችን ያነጋገረው አንድ ሙስሊም ፣ እኛ መንግስት እንደሚለው አሸባሪዎች ሳንሆን በመንግስት ኢፍትሀዊ ተግባር ተሸባሪዎች ነን፣ ሰላማዊ መሆናችንን ዛሬ ነጭ ለብሰን አሳይተናቸዋል ብሎአል

የፌደራል ፖሊስ አባላት በትላልቅ መኪኖች ላይ ሆነው ሲጠብቁ ታይተዋል።

የሙስሊም መሪዎች ቢታሰሩም ትግሉ እየተጠናከረ ከመሄድ ውጭ ፣ የመንግስት ባለስልጣናት እንደሚሉት እየቀዘቀዘ አልሄደም። የፌደራል ጉዳዮች ሚኒሰትር የሆኑት አቶ ሽፈራው ተክለማርያም ሰሞኑን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ሙስሊሙ ተረጋጋቶ ጸሎቱን እያካሄደ ነው በማለት ተቃውሞ እንደሌለ ለማሳመን ሞክረዋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide