መለስተኛ የበረራ ሰራተኞች ላይ እገዳ ተጣለ

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 22/2010)

የኢትዮጵያ አየር መንገድ መለስተኛ የበረራ ሰራተኞቹን ወደ አሜሪካና ካናዳ እንዳይበሩ እገዳ መጣሉ ተነገረ።

አየር መንገዱ የበረራ ሰራተኞቹ ወደ አሜሪካና ካናዳ እንዳይበሩ የከለከለው ወደ ሁለቱ ሀገራት የሚመጡ ባልደረቦቹ በመጡበት ጥገኝነት እየጠየቁ በመቅረታቸው ነው።

ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፈው ወር ብቻ 21 የበረራ ሰራተኞች ለስራ በወጡበት በካናዳና አሜሪካ ቀርተዋል።

እናም የአየር መንገዱ መለስተኛ የበረራ ሰራተኞች በተለይ በአሜሪካና በካናዳ ለስራ እንደወጡ በዛው ሳይመለሱ መቅረታቸውን ተከትሎ ከእንግዲህ ወደዛ በሚደረጉ በረራዎች ላይ መለስተኛ የበረራ ሰራተኞች  እንዳይሰማሩ ድርጅቱ እገዳ እንደጣለባቸው ፎርቹን ዘግቧል።

አየር መንገዱ ይህን እገዳ ሲጥል ስራው በማንና እንዴት እንደሚተካ የገለጸው ነገር ግን የለም።

ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰራተኞች ብዙዎቹ ለበረራ ወደ ውጭ ሲወጡ የኮንትሮባንድ እቃ በማመላለስ በሕገወጥ ንግድ ስራ ተሰማርተው መገኘታቸውን ተከትሎ እቃ እንዳያመላልሱ መከልከላቸው ይታወሳል።

አሁን ደግሞ በኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚሰሩ መለስተኛ የበረራ ሰራተኞች አሜሪካና ካናዳ መጓዝ እንደማይችሉ መመሪያ ወጥቷል።

በአየር መንገዱ ለበረራ ወደ ውጭ የሚመደቡ ሰራተኞች የ5 መቶ ሺ ብር ዋስትና እንዲያመጡ ይገደዳሉ።

እናም ከአየር መንገዱ ጋር በሰራተኝነት በረው የሚጠፉ ሰራተኞች የስያዙትን የዋስትና ገንዘብ እንደሚያጡ ነው የሚነገረው።

በኢትዮጵያ አየር መንገድ በዘር መድልኦ ምክንያት በርካታ ሰራተኞች ስራ ለመልቀቅ እንደሚገደዱ ነው የሚነገረው።

በአየር መንገዱ የትግራይ ተወላጆች ከጽዳት እስከ ዋና ስራ አስፈጻሚ ድረስ በብዛት እንደሚገኙ ብዙዎቹ ይመሰክራሉ።

እናም በአድልኦና በቢሮክራሲያዊ ትጽእኖዎች ሳቢያ አየር መንገዱን እየለቀቁ የሚሄዱ ሰራተኞች መበራከታቸው ይነገራል።