ሕሙማን የሚፈልጉትን መድሃኒት ባለማግኘታቸው ችግር ላይ መውደቃቸው ተሰማ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 29/2010)

በኢትዮጵያ በውጭ ምንዛሪ እጥረት ሕሙማን የሚፈልጉትን መድሃኒት ባለማግኘታቸው ችግር ላይ እየወደቁ መሆኑን ቢቢሲ ዘገበ።

መድሃኒት አስመጪዎች የውጭ ምንዛሪ ማግኘት ባለመቻላቸው በተለይ የልብና የስኳር ህሙማን የሚፈልጉትን መድሃኒት ለማግኘት ተቸግረዋል።

ቢቢሲ በአዲስ አበባ ተዘዋውሮ ያነጋገራቸው ህሙማን የሚፈልጉትን መድሃኒት ማግኘት ባለመቻላቸው ችግር ላይ እየወደቁ መሆኑን ጠቁመዋል።

በተለይም የስኳርና የልብ ህሙማን እለት እለት መድሃኒት የሚፈልጉ ቢሆንም በየመድሃኒት ቤቶቹ ዞረው ማግኘት አልቻሉም።

ለቢቢሲ አስተያየቱን የሰጠው ግሩም ፈለቀ የተባለ የስኳር ህመምተኛ ካለፉት 3 ወራት ወዲህ በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች የኢንሱሊን እጥረት እንዳጋጠመው ነው የገለጸው።

መድሃኒቱ ቢገኝ እንኳ በውድ ዋጋ የሚሸጥበት ሁኔታ ተፈጥሯልም ሲል ምሬቱን ይገልጻል።

በተለይም በግል መድሃኒት ቤቶች የስኳር ሕመም መድሃኒት ማግኘት አዳጋች እየሆነ መምጣቱን ተጠቃሚዎች ገልጸዋል።

ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የአንድ ግዙፍ የመድሃኒት አስመጪ ኩባንያ ምክትል ዳይሬክተር እንዳሉትም በአጠቃላይ በመድሃኒት ላይ ያለው እጥረት ዋነኛው ችግር የውጭ ምንዛሪ ነው።

ከዚህ በፊት ጊዜ የማይሰጡ እንደ ኢንሱሊን አይነት መድሃኒቶችን ለማስገባት ብሔራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሪ ይፈቅድ የነበረ ቢሆንም አሁን ግን ከልክሏል ብለዋል።

የመድሃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ተስፋ ሚካኤል አፈወርቅ በበኩላቸው እነዚህ መድሃኒቶች ለመንግስት ሆስፒታሎችና መድሃኒት ቤቶች በበቂ ሁኔታ እየቀረቡ ናቸው ብለዋል።

የግል አስመጪዎች በውጭ ምንዛሪ እጥረት ምክንያት መድሃኒት ባለማስገባታቸው ጫናው በመንግስት ላይ ወድቋል ባይ ናቸው።

ኢሳት ከጉዳዩ ጋር ቅርበት ያላቸውን ምንጮች ጠቅሶ እንደዘገበው በኢትዮጵያ ያለው አገዛዝ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት አጋጥሞታል።

በአሁኑ ጊዜም 7 መቶ ሚሊየን ዶላር ብቻ የመጠባበቂያ ክምችት ሲኖረው ይህም ለ3 ሳምንት ብቻ የሚበቃ መሆኑ ነው የተገለጸው።

ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ያጋጠመው የሀገሪቱ አገዛዝ ሜጋ ፕሮጀክቶችን እስከመሰረዝ መድረሱም ይነገራል።

ከዚሁም መካከል ከጅቡቲ አዲስአበባ ድረስ ይዘረጋል የተባለው የነዳጅ ማስተላልፊያ መስመር አንዱ ነው።

በጅቡቲ ወደብ የተጠራቀሙ ሸቀጦችም በነዳጅ እጥረት ምክንያት መንቀሳቀስ አለመቻላቸው ይነገራል።

ይህንኑ ችግር መሰረት በማድረግም የአለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ዋና ዳይሬክተር ክርስቲን ላጋርድ ይፋዊ ጉብኝት በኢትዮጵያ እንደሚያደርጉ የኢሳት ምንጮች መግለጻቸው ይታወሳል።

ሴትዮዋ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ መንግስት ኢትዮ-ቴሌኮምን የመሳሰሉ ትላልቅ የመንግስት ተቋማት ወደ ግል እንዲዞሩ ግፊት ሊያደርጉ ይችላሉ ተብሏል።