ልጃቸውን የገደለባቸው ተጠርጣሪ ለአሜሪካ ተላልፎ በመሰጠቱ እፎይታን ማግኘታቸውን ገለጹ

(ኢሳት ዲሲ–ሚያዚያ 23/2011)ልጃቸውን የገደለባቸው ተጠርጣሪ ለአሜሪካን ተላልፎ በመሰጠቱ እፎይታን ማግኘታቸውን ኢትዮጵያዊው ወላጅ አባት ገለጹ።

ከሁለት ዓመት በፊት በአሜሪካ ቨርጂኒያ ግዛት ሁለት ኢትዮጵያውያን በመግደል ወደ ኢትዮጵያ ሸሽቶ የነበረው ተጠርጣሪን ኢትዮጵያ አሳልፋ መስጠቷ በልጃችን ሞት የተሰበረውን ልባችንን የሚክስ ነው ሲል ወላጅ አባት አቶ ግርማ ዮሃንስ ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ ገልጸዋል።

እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በህዳር 2016 በአሜሪካ ቨርጂኒያ ስፕሪንግ ፊልድ በተባለ ከተማ ነዋሪ የሆኑ ሁለት ወጣቶችን በጥይት በመግደል የተሰወረ ተጠርጣሪ ዮሀንስ ነሲቡ በትላንትናው ዕለት ለአሜሪካ ተላልፎ መሰጠቱን የኢትዮጵያ ጠቅላይ አቃቤ ህግ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ዝናቡ ቱኑ ለኢሳት ማረጋገጣቸው ይታወሳል።

ለሁለት ዓመታት ክፍትህ ተደብቆ የቆየው የልጆቻችን ገዳይ በመጨረሻም ወንጀሉን በፈጸመበት ሀገር ለፍርድ መቅረቡ አስደስቶናል ብለዋል የሟች ሄኖክ ግርማ ወላጅ አባት።