ለኢህአዴግ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ የለገሰው ግለሰብ፧ በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ አጭበርብሯል የሚል ክስ ቀረበበት

ሚያዚያ ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም  

ኢሳት ዜና:-ዮሐንስ ሲሳይ የተባለው የ40 አመት ጎልማሳ ኢህአዴግ አገሪቱን ከተቆጣጠረ በሁዋላ በአጭር ጊዜ ቢሊየነር ለመሆን የበቃ የዘመኑ ባለሀብት ነው።

የሱ እና ሸበል የሚባሉ ኩባንያዎችን የመሰረተው ዮሐንስ ፣ ኢህአዴግ ለምርጫ በሚወዳደርበት ጊዜ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ለፓርቲው ለግሷል።

የትኛውም የአገር ውስጥ ባለሀብት ባላደረገው መልኩም፧ ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ በማውጣት ለአባይ ግድብ ማሰሪያ ቦንድ ገዝቷል።

ከኢህአዴግ ባለስልጣናት ጋር እጅና ጓንት በመሆን ቢሊዮነር ደረጃ የደረሰው ዮሀንስ፣ ያሬድ ከሚባለው የንግድ ሸሪኩና ከሌሎችም የኩባንያው ሰራተኞች ጋር በመሆን ያለፈውን አንድ ወር በማእከላዊ እስር ቤት አሳልፎአል።

በዮሀንስ እና በሸሪኮቹ  ላይ የቀረበው ክስ እንደሚያሳየው፧ ግለሰቡ እና ግብረ አበሮቻቸው ከ795 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆን ገንዘብ በታክስ ማጭበርበር ለግል ጥቅማቸው አውለዋል።

የብረታብረት ማቅለጫ ፋብሪካ ባለቤቶች የሆኑት ዮሀንስና ያሬድ፧ ድርጅታቸው በአመት 3 ቢሊዮን የሚጠጋ ገንዘብ የሚያንቀሳቅስ ቢሆንም፣ ለመንግስት ይፋ ያደረጉት ግን 2 ቢሊዮን ብር ገደማ ነው።

የፌደራል አቃቢ ህግ ባቀረበው ክስ፧ የሱ ኩባንያ ከ2000 እስከ 2003 ዓም ያልከፈለው ታክስ 200 ሚሊዮን ብር ይተጋል::

፣ኩባንያው; ከ2004 ዓም ጀምሮ  ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ኪሳራ እንደደረሰበት ለመንግስት ቢያሳውቅም:  አቃቢ ህግ እንደሚለው ግን  በ2004 ዓም ከ450 ሚሊዮን ብር በላይ ትርፍ አግኝቷል።

የ ተ ከሳሾቹን ጉዳይ የያዘው ስምንተኛው ወንጀል ችሎት ፧ተከሳሾች ላቀረቡት የዋስትና ጥያቄ ከአምስት ቀናት በሁዋላ መልስ እንደሚሰጥ ፎርቹን ዘግቧል።

በኢህአዴግ ደጋፊነታቸው የሚታወቁት አቶ ዮሀንስ፧ ለምን ታሰሩ የሚለው ጥያቄ የከተማው መነጋጋሪያ ሆኗል።

ብዙዎች የሚገምቱት ግለሰቡ ለኢህአዴግ መስጠት የሚገባውን ገንዘብ ባለመስጠቱ ነው የሚል ሲሆን፣ ሌሎች ወገኖች ደግሞ ከዚህ ቀደም ህወሀት ስታር ኩባንያንና የኢትዮጵያ  አማልጋሜትድ ሊሚትድን የመሳሰሉ ድርጅቶችን  አጥፍቶ ገበያውን በራሱ ድርጀቶች እንዳስያዘው ሁሉ፣ በአጭር ጊዜ ቢሊየነር የሆኑትን የአቶ ዮሀንስንና ሸሪኮቻቸውን ኩባንያዎች ከውድድር ውጭ በማድረግ ገበያውን ለመቆጣጠር አስቦ ሊሆን ይችላል ይላሉ።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide