ለስራ ወደ ውጭ ሃገራት መጓዝ የሚከለክለውን እግድ ተነሳ

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 23/2010)

መንግስት በገጠመው የውጭ ምንዛሪ እጥረት የተነሳ ለስራ ወደ ውጭ ሃገራት መጓዝ የሚከለክለውን እግድ ማንሳቱ ተገለጸ።

እግዱ የተነሳው የተቀመጡት ቅድመ ሁኔታዎች ሳይሟሉ በመቅረታቸው መሆኑን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

ከጥቅምት 2006 ጀምሮ ታግዶ የቆየው የውጭ ሀገራት የስራ ስምሪት ከጥር 22 ጀምሮ እንዲነሳ የሚኒስትሮች ምክር ቤት መወሰኑ ነው የታወቀው።

ምክር ቤቱ ውሳኔውን ሲያሳልፍ ደግሞ የተቀመጡት ቅድመ ሁኔታዎች አልተሟሉም የሚል ምክንያትን በማስቀመጥ ነው ሲሉ በሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ የሚገኙ የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

ምንጮቹ እንደሚሉት ከሆነ በ2008 ተሻሽሎ የወጣው የግል ስራና ሰራተኛ አዋጅ በአስገዳጅነት ያስቀመጣቸው ቅድመ ሁኔታዎች ነበሩ።

እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች የተጣሱት መንግስት ያጋጠመውን የውጭ ምንዛሪ ድርቅ መቋቋም ስላቃተው ያገኘውን ቀዳዳ በሙሉ ለመጠቀም ካለው ፍላጎት በመነጨ ነው ብለዋል።

በሌላ በኩል በእገዳው ምክንያት የግል ስራ አገናኝ ድርጅታቸው የተዘጋባቸው ግለሰብ ለኢሳት እንደገለጹት በእገዳውም ምክንያት ዜጎች በህገወጥ መንገድ ከፍተኛ ገንዘብ ከፍለው እንዲጓዙና እስከ ሞት የሚያደርስ አደጋ ላይ እንዲወድቁ ማድረጉን ተናግረዋል።

አሁንም ቢሆን በ2008 በወጣው አዋጅ የተቀመጡት ቅድመ ሁኔታዎች እስካልተነሱ ድረስ ሕገ ወጥ ስደቱ ተባብሶ እንደሚቀጥል አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

በአዋጁ መሰረት የግል ስራ አገናኝ ኤጀንሲ ሆኖ ለመስራት ፈቃድ የሚጠይቅ ኢትዮጵያዊ ከአንድ ሚሊየን ብር ያላነሰ ካፒታል እንደሚያስፈልገው አዋጁ ይደነግጋል።

በተጨማሪም ማንኛውም ኤጀንሲ ለሰራተኛ ደህንነት ዋስትና አንድ መቶ ሺ ዶላር ወይም ተመጣጣኙን የኢትዮጵያ ብር በዝግ ሒሳብ ባንክ ማስቀመጥ ይኖርበታል።

ለዋስትና በዝግ ሒሳብ የተቀመጠውን ገንዘብ መንግስት የመንግስት ግምጃ ቤት ሰነድ መግዣና የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴር በሚያወጣው መመሪያ መሰረት ለአትራፊና አዋጪ ተግባሮች ሊውል እንደሚችል በሕግ ተደንግጓል።