ህዝቡ ትግሉን አጠናክሮ እንዲቀጥል አርበኞች ግንቦት ሰባት ጥሪ አቀረበ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 5/2010)በህወሀት መንግስት የብሄራዊ ደህንነት ምክር ቤት የወጣው ዕቅድ የስርዓቱ የመጨረሻው ሙከራ በመሆኑ ህዝቡ ትግሉን አጠናክሮ እንዲቀጥል አርበኞች ግንቦት ሰባት ጥሪ አቀረበ።

ንቅናቄው ለኢሳት እንደገለጸው በስልጣን ላይ ያለው ስርዓት በውድቀት አፋፍ ላይ የሚገኝ በመሆኑ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የሚደረጉት ሁለገብ ትግሎችን ለማፋፋም ተዘጋጅቷል።

የህወሃት መንግስት በዕቅዱ ላይ በአሸባሪነት ከወነጀላቸውና ስርዓቱን በማስጨነቅ ብርቱ ፈተና እንደደቀኑ ከተጠቀሱት ድርጅቶች አንዱ አርበኞች ግንቦት ሰባት ንቅናቄ መሆኑ ይታወቃል።

ሾልኮ የወጣውና በመንግስት የቀረበው ወቅታዊ ሁኔታን የሚዘረዝረው ዕቅድ ሀገሪቱ ያለችበትን አደጋ በጥልቀት የሚያሳይ ነው።

የህወሀት መንግስት በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በጸጥታና ደህንነት የገጠሙ አደጋዎች ህዝቡን ተስፋ እንዳስቆረጡት የገለጸበት ዕቅድ ግብጽንና ኤርትራን ድጋፍ በመስጠት የሚከስ ነው።

አርበኞች ግንቦት ሰባት ንቅናቄንና የኦሮሞ ነጻነት ግንባርን በሀገሪቱ ለተፈጠሩት ቀውሶች ዋነና ተጠያቂ ያደርጋል።

ዕቅዱ ላይ የተጠቀሱት ሁለቱ ድርጅቶች በሀገሪቱ ውስጥ እንደፈለጉ እየፈነጩ በመሆኑ የህዝብ ደህንነት ስጋት ላይ ወድቋል ይላል የህወሀት መንግስት።

ኢሳት በዕቅዱ ላይ ክስ የቀረበባቸውን ሁለቱን ድርጅቶች ለማግኘት የሞከረ ሲሆን ለጊዜው የኦሮሞ ነጻነት ግንባር አመራሮችን ለማነጋገር ያደረገው ሙከራ አልተሳካም።

የአርበኞች ግንቦት ሰባት ንቅናቄ ከፍተኛ አመራርና የውጭ እንቅስቃሴዎች አስተባባሪ አቶ ነአምን ዘለቀ እንደሚሉት የወጣው እቅድ የህውሀት መንግስት ከውድቀት አፋፍ ላይ እንደሚገኝ የሚያሳይ ነው።

ይህንን ለመሻገር ደግሞ በቀቢጸ ተስፋ የግድያ ርምጃዎችን በስፋት ለማከናወን እየተዘጋጀ መሆኑን የሚያመለክት ነው ብለዋል።

የህወሀት የበላይነትን ለማስቀጠል እንጂ ከዚያ ያለፈ ትርጉም የለውም ይላሉ አቶ ነአምን ዘለቀ።

በኢትዮጵያ የጅምላ ግድያ ጄኖሳይድ እንደተፈጸመ በተገለጸበት በዚሁ እቅድ ግጭቶቹ ሀገራዊ መልክ መያዛቸውንና ቀጣይነት ያላቸው መሆናቸውን የህወሃት መንግስት በስጋት ይገልጻል።

የፌደራል ስርዓቱ አደጋ ላይ መውደቁንና ስርዓት አልበኝነትና እምቢተኝነት እየተስፋፉ መሆናቸውን የገለጸው የህወሀት መንግስት ህዝቡ በመንግስት ተስፋ ቆርጧል ሲል የመጣበትን አደጋ በዝርዝር አስቀምጧል።

ከፍተኛ ገንዘብ ለጦርነት እየተሰበሰበ ነው፥ የመንግስት ተቃውሚዎች ህዝቡን በጎናቸው እያሰለፉ ነው፥ የጸጥታ ሃይሉ በመንግስት ተስፋ እየቆረጠ መሆኑን የገለጸው የህወሀት መንግስት ይህን የሚቀለብስ አፋጣኝ ርምጃ ካልወሰድን አደጋው ከባድ ነው ብሏል።

የአርበኞች ግንቦት ሰባት ንቅናቄ እያደረገ ያለውን ትግል አጠናክሮ እንደሚቀጥልና የኢትዮጵያ ህዝብ በውድቀት አፋፍ ላይ ያለውን ስርዓት ነቅሎ ለመጣል እንዲዘጋጅም ጥሪ አቅርቧል።