ሁለት የአረና አባላት የድርጅቱን ልሳን ሲበትኑ ተያዙ

ታህሳስ ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-አረና ፓርቲ በየሶስት ወሩ ማሳተም የጀመረውን የድርጅቱን ልሳን ሲያሰራጩ የተገኙ 2 የድርጅቱ አባላት በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸውን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

የመቀሌ የአረና  ጽህፈት ቤት ተጠሪ የሆኑት አቶ ሱልጣን ህህሸ ለኢሳት እንደተናገሩት አቶ አያሌው በየነና አቶ ተካልኝ  ታደሰ የተባሉት ድርጅቱ አባላት የተሳሩበት ምክንያት የፓርቲውን መታወቂያ አልያዛችሁም ተብለው ነው። ይሁን እንጅ ፓርቲው እስረኞቹ የድርጅቱ አባላት መሆናቸውን ለአካባቢው ፖሊስ መግለጹን አቶ ሱልጣን ተናግረዋል።

ትናንት ሰኞ እለትም በሁመራ አደላይ ቀበሌ ሌላው አባላቸው ወረቀት ሲበትኑ መያዛቸውን ፣ የጽህፈት ቤታቸው ሰንደቅ አላማ የሚውለበለብበት ምሰሶ መሰረቁንም ገልጸዋል።

በአረና ትግራይ አባላት ላይ የሚፈጸመው እንግልት እየጨመረ መምጣቱን ድርጅቱ በተደጋጋሚ መግለጹ ይታወሳል።

በጉዳዩ ዙሪያ የሽራሮ ፖሊስ አመራሮችን ለማግኘት ሙከራ ብናደርግም አልተሳካልንም።