ፕሬዝዳንት ሳህለ ወርቅ ከዓለማችን 100 ተጽዕኖ ፈጣሪ ሴቶች መካከል ተቀመጡ

(ኢሳት ዲሲ–ሕዳር 28/2011) ከዓለማችን 100 ተጽዕኖ ፈጣሪ ሴቶች ውስጥ የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ሳህለ ወርቅ ዘውዴ በ97ኛ ደረጃ ላይ ተቀመጡ።

የጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ መርክል የአለማችን 1ኛ ተጽዕኖ ፈጣሪ ሴት ሆነው ሲመዘገቡ የብሪታኒያዋ ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሳ ሜይ የአለማችን ሁለተኛዋ ተጽዕኖ ፈጣሪ ናቸው ሲል ፎርብስ ዘግቧል።

በቢዝነስና ፋይናንስ ጉዳዮች ላይ ይበልጥ ትኩረት የሚያደርገው ፎርብስ መጽሔት የ2018 ተጽዕኖ ፈጣሪ በማለት የ200 እንስቶችn ዝርዝር ይፋ ባደረገበት መረጃ የአይ ኤም ኤፍ ዳይሬክተርን ፈረንሳይቷን ክርስቲን ላጋርድን በስምንተኛ ደረጃ አስቀምጧል።

በቴክኖሎጂ መስክ የቪዲዮዎች ቋት የሆነውና የ90 ቢሊዮን ዶላር ንብረት ባለቤት የሆነው youtube ዋና ስራ አስፈጻሚ ሱዛን ዋጂኪን በ7ኛ ደረጃ ያስቀምጣል ፎርብስ የባለጸጋው ቢልጌት ባለቤትና የሚሊንዳ ጌት ፋውንዴሽን መስራች የሆኑትን ለጋሷን ሜሊንዳ ጌትን በ6ኛ ደረጃ አስቀምጧል፡።

ታዋቂዋን የቲቪ ሾው አዘጋጅና ቢሊየነር የሆነችውን ኦፕራ ዊን ፍሬይን በ20ኛ ደረጃ ተጽዕና ፈጣሪ ሴት በማለት ያስቀመጠው ፎርብስ ለእንግሊዝም ንግስት ኤልዛቤት 23ኛ ደረጃን ሰጥቷል።

የኒውዝላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ጃሲንዳ ኦርዶርን 29ኛ ደረጃ የሰጠው ፎርብስ የኖርዌይዋን ጠቅላይ ሚኒስትር ኦርና ሶልበርግን 35ኛ የክሮሺያውን ፕሬዝዳንት ኮሊንዳ ጋርባርን 47ኛ የሊቱኒያን ፕሬዝዳንት ዳልያ ግራይባውስኪትን 63ኛ የኦስቶኒየን ፕሬዝዳንት ክርሲ ካልጁላይድን 76ኛ የሰርቢያ ጠቅላይ ሚኒስትር አና ብራና ቢክን 91ኛ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ሲል ፎርብስ ዘርዝሯል።

የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት የሆኑት ወይዘሮ ሳህለወርቅ ዘውዴን ከ100 ተጽዕኖ ፈጣሪ ሴቶች 97 ደረጃ ላይ አስቀምጧል።