ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የሆላንድ ጉዞው ቢስተጓጎልም በመጨረሻ በግብዛ ቦታው ላይ እንደሚገኝ ታወቀ

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የሆላንድ ጉዞው ቢስተጓጎልም በመጨረሻ በግብዛ ቦታው ላይ እንደሚገኝ ታወቀ
(ኢሳት ዜና ሚያዝያ 12 ቀን 2010 ዓ/ም) በሆላንድ አምስተርዳም በሚከበረው የአምነስቲ ኢንተርናሽናል 50 ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል የክብር እንግዳ ሆኖ የተጋበዘው ጋዜጠኛና የነጻነት ታጋይ እስክንድር ነጋ ለበረራ እየተዘጋጀ ሳለ ከቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ፓስፖርቱን ተነጥቆ ከሀገር እንዳይወጣ መከልከሉ በኢትዮጵያውያን ዘንድ ቁጣ ቀሰቀሰ።
ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ ነገ ቅዳሜ ቀትር ላይ በሚጀመረው የአምነስቲ በዓል ላይ ለመገኘት ትናንት ምሽት ቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ደርሶ በረራውን ሲጠብቅ የደህንነት ሰዎች ፓስፖርቱን የቀሙት ሲሆን፣ “በመንግስት ላይ ሌላ ወቀሳ እንዳያስከትል ለበላይ አካል አሳውቁልኝ ሲላቸው፣ ትዕዛዙ የመጣው ከበላይ አካል ነው የሚል ምላሽ እንደሰጡት ገልጿል።
የእስክንድር የመንቀሳቀስ መብት መከልከል መሰማቱን ተከትሎ በርካታ ኢትዮጵያውያን በማህበራዊ ሚዲያ ቁጣቸውን ሲገልጹ የዋሉ ሲሆን፣የአምነስቲ ኢንተርናሽናል ሰዎችም በጉዳዩ ዙሪያ የኢትዮጵያ መንግስትን ማነጋገራቸው ታውቋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ዛሬ ማርፈጃው ላይ ወደ ቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ተጠርቶ በቀሙት ሰዎች የጉዞ ሰነዱ እንደተመለሰለትና መጓዝ እንደሚችል እንደተገለጸለት እስክንድር ተናግሯል።
በመሆኑም ለነገው የአምነስቲ ኢንተርናሽናል ዝግጅት ለመድረስ ማምሻውን ከአዲስ አበባ የተነሳ ሲሆን፣ ነገ ከጧቱ 4 ሰዓት በክብር እንግድነት የሚገኝበት ዝግጅት ከሚጀመርበት 2 ጸዓታት ቀድሞ አምስተርዳም ስኪፖል አውሮፕላን ማረፊያ እንደሚደርስ ታውቋል።
በሆላንድ እና አካባቢው ያሉ ኢትዮጵያውያንም ባሰናዱት ዝግጅት የነጻነት ታጋዩን እስክንድር ነጋን የፊታችን እሁድ ያከብሩታል።