ዶክተር አብይ ደፋር የለውጥ ርምጃዎችን እንዲወስዱ ጥሪ ቀረበ

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 20/2010) ደፋር የለውጥ ርምጃዎችን ውሰድ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ከጎንህ ነው

የቀድሞው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩት ሚስተር ኽርማን ኮኽን  ዶክተር  አብይ ደፋር የለውጥ ርምጃዎችን እንዲወስዱ ጥሪ አቀረቡ።

ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ከጎናቸው እንደሆነም አረጋግጠዋል።

የአፍሪካ ሕብረት የወቅቱ ሊቀመንበር እና የሩዋንዳው ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜም በአፍሪካ ሕብረት  እና በአፍሪካ መሪዎች ስም የደስታ መግለጫ አስተላልፈዋል።

ኢትዮጵያም በአፍሪካ  አህጉር ታሪካዊ እና ወሳኝ ሚናዋን በቅርቡ  ዕውን እንደምታደርግም ዕምነታቸውን ገልጸዋል።

በአሜሪካ የወጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት  የአፍሪካ ረዳት ሚኒስትር የነበሩት ሚስተር ኸርማን ኮኽን በማህበራዊ ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ዶክተር አብይ ደፋር የለውጥ  ርምጃዎችን እንዲወሰዱ ጥሪ አቅረበዋል።

መልዕክት ለአዲሱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በማለት ጥሪያቸውን ያቀረቡት ኽርማን ኮኽን መጪው ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ   ወደ ዲሞክራሲያዊ ለውጥ ደፋር ርምጃዎችን እንዲወስዱና እንዳያመነቱ አሳስበዋል።

ኢኮኖሚውን እና ፖለቲካውን  ጠቅልለው የያዙት የሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ አጭበርባሪ  መሪዎች ማንነታቸው  ስለተጋለጠ ሊገትሁ አይችሉም ፣አለም አቀፉ ማህበረሰብ ከጎንህ ነው” ሲሉ ኸርማን ኮኸን መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

በጆርጅ ኽርበርት ቡሽ ዘመነ  መንግስት በአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ  ረዳት ሚኒስትር የነበሩት ሚስተር ኸርማን ኮኽን  የደርግ መንግስት ሊወድቅ አንድ ቀን ሲቀረው በለንደን የተካሄደውን ድርድር የመሩ መሆናቸው ይታወሳል።

የለንደኑ ድርድር በደርግ መንግስት፣በሻዕቢያ፣በኢሕአዴግ እና በኦነግ መካከል እንደነበር አይዘናጋም።

የደርግ መንግስትን ልኡካን በመምራት በድርደሩ የተሳተፉት ጠቅላይ ሚኒስትር ተስፋዬ ዲንቃ ድርደሩ በጓሮ በር  ያለቀ ነው በማለት መግለጫ መሰጠታቸውም ይታወሳል።

ይህ በእንዲህ እንዳለም ዶክተር አብይ አህመድ ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒስትር እንዲሆኑ በኢሕኣዴግ ሊቀመንበርነት በመመረጣቸው ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜ የደስታ መግለጫ አስተላልፈዋል።

የወቅቱ የአፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበር የሆኑት የሩዋንዳው ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜ በማህበራዊ ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ለዶክተር  አብይ ስልክ በመደወል ደስታቸውን ለርሳቸው ፣ለኢሕአዴግ እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ማስተላለፋቸውን አመልክተዋል።

እንደ አፍሪካ ሕብረት ሊቀመንበርነታቸው በአፍሪካ ሕብረት እና በመላው የአፍሪካ መሪዎች ስም  አጋርነታቸውን የገለጹት ፕሬዝዳንት ፖል  ካጋሜ  ኢትዮጵያውያን ለገጠማቸው ችግር በመፍትሄ ጥረቱ  እንዲቀጥሉም ጥሪ አርበዋል።

ኢትዮጵያ ታሪካዊ እና ወሳኝ ሚናዋን  በአህጉራችን  አፍሪካ  በቅርቡ ዕውን እንደምታደርግም ዕምነታቸውን ገልጸዋል።