የግጭት ነጋዴዎችን ሴራ እናክሽፍ ተባለ

(ኢሳት ዲሲ–መስከረም 2/2011) የግጭት ነጋዴዎችን ሴራ እናክሽፍ ሲሉ የጠቅላይ አቃቤ ህግ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ጥሪ አደረጉ።

ሃላፊው አቶ ታዬ ደንደአ በግል የማህበራዊ መድረካ ላይ ባስተላልፉት ጥሪ ኢትዮጵያውያን ከትንንሽ አጀንዳዎች ወጥተው ስለሀገር ከልብ እንዲያስቡ ጠይቀዋል።

አቶ ታዬ ይህን መልዕክት ያስተላለፉት ዛሬ በአዲስ አበባ ከሰንደቅ ዓላማና አርማ ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን መለስተኛ ግጭት ተከትሎ ነው።

የኦሮሞ ነጻነግ ግንባር መሪ አቶ ዳውድ ኢብሳን ለመቀበል ዝግጅት በማድረግ ላይ ባሉ የኦሮሞ ወጣቶችና በአዲስ አበባ ነዋሪዎች መካከል በተፈጠረ ግጭት የመኪና መሰባበር አደጋ የደረሰ ሲሆን ፖሊስ በአስለቃሽ ጢስ ተጠቅሞ ግጭቱን ማብረዱን የደረሰን መረጃ ያመልክታል።

የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ታዬ ደንደአ ሀገር ከሌለ የሰንደቅዓላማና ሀውልት ጉዳይ ትርጉም የለውም ሲሉ በመልዕክታቸውን አስፍረዋል።

ችግራችን በባንዲራ ወይም በሃዉልት አይፈታም ያሉት አቶ ታዬ ደንደአ የግጭት ነጋዴዎችን ሴራ እናክሽፍ ሲሉ ጥሪ አድርገዋል።