የሶማሌው ክልል ርዕሰ መስተዳድር አብዲ ኢሌ፣ ሂዩማን ራይትስ ዎች ያወጣባቸውን መግለጫ እንዲያስተባብል ያስገደዱትን በቅርበ የተፈታ እስረኛ “በበቂ ሁኔታ አላስተባበለም”በማለት ዳግም እንዲታሰር አዘዙ። ( ኢሳት ዜና ሃምሌ 3 ቀን 2010 ዓ/ም ) የእስርት ዕዛዝ የወጣበት ሙሀመድ አብዱላሂ ጉዴ ሕይወቱን ለማትረፍ ከአካባቢው ተሰውሯል።

የሶማሌው ክልል ርዕሰ መስተዳድር አብዲ ኢሌ፣ ሂዩማን ራይትስ ዎች ያወጣባቸውን መግለጫ እንዲያስተባብል ያስገደዱትን በቅርበ የተፈታ እስረኛ “በበቂ ሁኔታ አላስተባበለም”በማለት ዳግም እንዲታሰር አዘዙ።
( ኢሳት ዜና ሃምሌ 3 ቀን 2010 ዓ/ም ) የእስርት ዕዛዝ የወጣበት ሙሀመድ አብዱላሂ ጉዴ ሕይወቱን ለማትረፍ ከአካባቢው ተሰውሯል።
ዓለማቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ሂዩማን ራይትስ ዎች ከጥቂት ቀናት በፊት ባወጣው መግለጫ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ በአቶ አብዲ ኢሌና በሶማሌ ክልል የደህንነት ባለሥልጣናት ላይ በአስቸኳይ ምርመራ እንዲያደርጉ ማሣሰቡ ይታወቃል።
ሂዩማን ራይትስ ዎች “የሞቱትን እንመስላለን” በሚል ርዕስ ባወጣወ በዚሁ ባለ 88 ገጽ መግለጫ፣ በአቶ አብዲ ኢሌ ትዕዛዝ አማካይነት በኦጋዴ እስር ቤቶች ሲፈጸሙ የቆዩትን ዘግናኝ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን የዓይን ምስክሮችን ዋቢ በማድረግ በዝርዝር አትቷል።
በሰው ልጆች ላይ ለተፈጸሙት አሰቃቂ ወንጀሎችም አቶ አብዲ ኢሌን ጨምሮ ከፍተኛ ባለሥልጣናትና የደህንነት ሠራተኞች ተጠያቂ መሆናቸውን ሂዩማን ራይትስ ዎች አስታዉቋል።
በኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን የሚፈጽሙ ባለሥልጣናትን በዝምታ የማለፍን ባህል ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ በመስበር ወንጀለኞቹን ለህግ እንዲያቀርቡም የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ በአጽንዖት አሣስቧል።
ይህን የሰብዓዊ መብት ተቋሙን ሪፖርት ተከትሎ ከፍ ያለ መረበሽ ውስጥ መግባታቸው የሚነገረው የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አብዲ ኢሌ ፣ባለፉት ቀናት የቀረበባቸውን ክስ ለማስተባበል ሲሞክሩ ቆይተዋል።
አብዲ ኢሌ በዚህ ሳያቆሙ ባለፉት ዓመታት በኦጋዴን እስር ቤቶች ከፍ ያለ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሢፈጸምባቸው የቆዩትንና በቅርቡ ከእስር የተፈቱትን እስረኞች መግለጫውን እንዲያስተባብሉ ማስገደድ ጀምረዋል።
በዚህ ዙሪያ በርዕሰ መስተዳድሩ አደጋ ከተጋረጠባቸው መካከል በብዙዎች ዘንድ ፡ሙሀመድ አኒ” ተብለው የሚጠሩት የቀድሞው የኦጋዴ ብሔራዊ ነጻነት ግንባር ኮማንደር ሙሀመድ አብዱላሂ ጉሌድ አንዱ ናቸው።
ከዓመታት በፊት ተይዘው ከሌሎች 1500 የኦብነግ ወታደሮች ጋር በክልሉ በሚገኝ አስከፊ ማሰቃያ እስር ቤት በሰቆቃ ያሳለፉት፣ የዛሬ አራት ወር ከእስር ሢለቀቁ “አሸባሪ ነበርኩ” ብለው በቪዲዮ እንዲቀረጹ የተገደዱት እና በእስር ቆይታቸው በተፈጸመባቸው ድብደባ ሁለት እጃቸውን የተሰበሩት ኮማንደር ሙሀመድ አኒ አሁንም ከአብዲ ኢሌ ጋር የአዳኝና ታዳኝ ትራጄዲ ወጥመድ ውስጥ ገብተዋል።
የዓይን እማኞች እንደሚሉት፣ አቶ አብዲ ኢሌ በትናንትናው ዕለት ፖሊሶንችንና ጋዜጠኞችን ወደ ኮማንደር ሙሀመድ አኒ በመላክ በሂዩማን ራይትስ ዎች የወጣው ሪፖርት ውሸት እንደሆነ በቢቢሲ የሶማሊኛ ፕሮግራም ቀርበው እንዲያስተባብሉ ያዟቸዋል።
የሙያ ሥነ ምግባራቸውን የጣሱት የቢቢሲ የሶማሊኛ ፕሮግራም ጋዜጠኞችም በታዘዙት መሰረት ከልዩ ፖሊሶች ጋር በመምጣት ኮማንደር መሀመድ አኒን በእስር ቤት ስለነበረው አያያዝ ቃለ ምልልስ ያደርጓቸዋል።
የዓይን እማኞች እንደሚሉት በአብዲ ኢሌ ማስፈራሪያ የደረሳቸው ኮማንደሩም በእርሳቸው ላይ ምንም እንዳልተፈጸመ፣ ስለ ሌሎች እስረኞች ጉዳይ ግን የሚያውቁት እንደሌለ ምላሽ ይሰጣሉ።
ኮማንደሩ የአስገድዶ መድፈር ወንጀልን ጨምሮ በሰብዓዊ መብት ተቋሙ የተዘረዘሩ ወንጀሎችን እንዲያስተባብሉ ቢገደዱም፣ በሌሎች ላይ የተፈጸመን ወንጀል ለማስተባበል ህሊናቸው ስላልፈቀደላቸው “ በተባሉት ጉዳዮች ዙሪያ የማውቀው ነገር የለም” የሚል መልስ መስጠታቸው እና የተጠበቀውን ያህል አለማስተባበላቸው አቶ አብዲ ኢሌን ለከፍተኛ ብስጭት ይዳርጋቸዋል።
ልክ ቃለ ምልልሱ እንዳለቀም፣ ከጋዜጠኛው ጋር የመጣው የልዩ ፖሊስ ኃይል አባል ከአቶ አብዲ ኢሌ የስልክ ትዕዛዝ በመቀበል ኮማንደሩን በህግ እንደሚፈለጉና ለዛሬ ጧት ፖሊስ ጣቢያ በመሄድ ሪፖርት እንዲያደርጉ ያስጠነቅቃቸዋል።
ይሁንና ኮማንደሩ የፖሊስ መጥሪያ እንደደረሳቸው የሰሙ የክልሉ አክቲቪስቶች በፍጥነት በመተባበር ትናንት ሌሊት ሌሊት ኮማንደሩን ከደገሀቡር ወደ አዲስ አበባ አስመልጠዋቸዋል።
ለያዥ ለገራዥ ያስቸገሩት እና ይህን የመሰወር ዜና የሰሙት ፈላጭ ቆራጩ አብዲ ኢሌም ፣ ኮማንደር ሙሀመድ አኒን ከአዲስ አበባ በማገት ወደ ጅግጅጋ አፍነው የሚወስዱ ደህንነቶችን ዛሬውኑ መላካቸው ታውቋል።
ይሁንና ፣ ጉዳዩን በቅርበት እየተከታተሉ ያሉ የኢሳት ምንጮች እንዳሉት፣ኮማንደሩን ለደህንነታቸው አስተማማኝ በሆነ ቦታ ናቸው።
በሕወሓት ጀነራሎች የሚደገፉት አብዲ ኢሌ በክልላቸው ከሚጽሟቸው አስከፊ የሰብ ዓዊ መብት ጥሰቶች ባሻገር ከሶማሌ ክልል ለተፈናቀሉ አንድ ሚሊዮን ኦሮሞዎችም ዋነኛ ተጠያቂ ቢሆኑም፣ እስካሁን በህግ ተጠይቀው አያውቁም።