የሲዳማ ዞን ክልል የመሆን ጉዳይን የሚጠይቅ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሄደ

(ኢሳት ዲሲ–የካቲት 14 /2011)የሲዳማ ዞን ክልል የመሆን ጥያቄን በህገ መንግስቱ መሰረት ተግባራዊ እንዲሆን የሚጠይቅ ሰላማዊ ሰልፍ በሀዋሳ ከተማ ተካሄደ።

በሲዳማ ዞን በሚገኙ 36 ወረዳዎችና ከተማ አስተዳድሮች የተውጣጡ ነዋሪዎች የተሳተፉበት ሰላማዊ ሰልፍ ሕገምንግስቱ ይከበር የሚል ጥያቄ አቅርበዋል።

የደቡብ ክልል ምክር ቤት በጥቅምት ወር ባካሄደው መደበኛ ጉባኤ የሲዳማ ዞን ክልል የመሆን ጥያቄ ህገ መንግስታዊ ሂደቱን ተከትሎ እንዲፈጸም ባለፈው ጥቅምት ወር ባካሄደው ጉባኤ መወሰኑ ይታወሳል።

ይሕም ሆኖ ግን ወሳኔውን ተከትሎ ሕዝበ ውሳኔ መደረግ ቢኖርበትም ሂደቱ ለምን ዘገየ በሚል የሲዳማ ዞን ክልል የመሆን ጥያቄ በህገ መንግስቱ መሰረት ተግባራዊ ይሁን የሚል ሰላማዊ ሰልፍ በሀዋሳ ከተማ ተካሄዷል።

በሰላማዊ ሰልፉ ላይ የሲዳማ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ቃሬ ጫውቻ፣ የሀዋሳ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ ስኳሬ ሹዳ እና የወጣቶች ተወካይ ንግግር አድርገዋል።

የሲዳማ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ቃሬ ጫውቻ፥ የሲዳማ ህዝብ በክልል ተዋቅሮ ራስን የማስተዳደር ጥያቄ ማቅረብ ከጀመረ ረጅም ዓመታትን ማስቆጠሩን ገልጸዋል።

በመሆኑም የሲዳማ ህዝብ የክልልነት ጥያቄ በህገመንግስቱ መሰረት ምላሽ መሰጠት እንዳለበትም አቶ ቃሬ ጫውቻ ገልፀዋል።

የሲዳማ ህዝብ ክልል ለመሆን እያቀረበ ያለው ጥያቄው በህገ መንገስቱ መሰረት በአፋጣኝ መልስ ማግኘት ያለበት ጉዳይ ነውም ብለዋል።

የሰላማዊ ሰልፉ ተሳታፊዎች “ህገ መንግስታዊ መብታችን ይከበር! የሲዳማ የክልልነት ጥያቄ መልስ ይሰጠው! የሪፈረንደም ቀን ይወሰን !” የሚሉና ሌሎች መፈክሮችን ይዘው ወጥተዋል።

ጥዋት ላይ መነሻውን ከሀዋሳ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ ያደረገው ሰላማዊ ሰልፉ መዳረሻውን ሀዋሳ ዓለም አቀፍ ስታዲዮም ላይ በማድረግ ተካሂዷል።

በህገ መንግስት መሰረት ክልል የመሆን ጥያቄ የሚያቀርበው ብሄር፣ ብሄረሰብ ወይም ህዝብ በወከለው ምክር ቤት በሁለት ሶስተኛ ድምፅ ተቀባይነት ማግኘት ይኖርበታል።በዚሁም መሰረት የሲዳማ ዞን ምክር ቤት ይህንን ክልል የመሆን ጥያቄን ባለፈው ዓመት ተቀብሎ ማፅደቁ የሚታወስ ነው።

ጥያቄው ለክልሉ ምክር ቤት ባለፈው ጥቅምት ወር ቀርቦ ወሳኔ ያገኘ ቢሆንም  ህዝበ ውሳኔ በጠየቂው ዞን የሚካሄድበትን ጊዜ እና ሁኔታን ገና አለማሳወቁ ተዘግቧል።በደቡብ ክልል ወላይታ፥ ከምባታና ጠምባሮ፥ጉራጌ እንዲሁም ከፍቾ ተመሳሳይ ክልል የመሆን ጥያቀ ማቅረባቸው ይታወሳል ።