የሕወሃቱን እጩ ለማስመረጥ አገዛዙ ጣልቃ እየገባ ነው

(ኢሳት ዲሲ–ታህሳስ 25/2010)

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንትን ለመምረጥ ውድድር ይካሄዳል ቢባልም የሕወሃቱን እጩ ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሃናን ለማስመረጥ አገዛዙ ጣልቃ እየገባ መሆኑን ምንጮች ገለጹ።

ለአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንትነት 22 እጩዎች ለውድድር ከቀረቡ በኋላ ዘጠኙ ለሁለተኛ ዙር ማለፋቸውን ለማወቅ ተችሏል።

በሕወሃት በኩል የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንት እንዲሆኑ ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሃና ተመራጭ ሲሆኑ መልማይ ኮሚቴው በአገዛዙ በኩል ግፊት እየተደረገበት መሆኑ ተገልጿል።

በኦሕዴድ በኩል ደግሞ ከፍልስፍና ዲፓርትመንት ዶክተር በቀለ ጉተማ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንት እንዲሆኑ ፍላጎት መኖሩንም ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

በሕወሃት በኩል ፕሬዝዳንት እንዲሆኑ የታጩት ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሃና በአሁኑ ጊዜ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኢኮኖሚክስ ዲፓርትምነት ሃላፊ ናቸው።

ለአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንትነት እየተወዳደሩ ካሉት መካከልም የጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ወንድም ፕሮፈሰር ፍቅሬ ደሳለኝም ይገኙበታል።