ኢትዮጵያዊ ዜግነት ያላቸው ግለሰብ ክስ ተመሰረተባቸው

(ኢሳት ዲሲ–መስከረም 15/2011) ኢትዮጵያዊ ዜግነት ያላቸው ግለሰብ የኬንያ ፖርላማ አባል ሆነዋል በሚል ክስ ተመሰረተባቸው።

የፓርላማ አባሏ ወንበራቸውን ተነጥቀው በምትካቸው ሌላ ሰው እንዲመረጥም ጥሪ ቀርቧል።

የመርሳን ቤት አውራጃን ወክለው የኬንያ ፓርላማ አባል የሆኑት ሶፍያ ሼክ ኡደን ከኬንያ ባሻገር የኢትዮጵያና የአሜሪካ ዜግነት ይዘዋል የሚል ክስ ቀርቦባቸዋል።

የመርሳ ቤት አውራጃ ነዋሪ የሆኑት ያያ መሃመድ ሃሰን ለኬንያ ከፍተኛው ፍ/ቤት በትናንትናው ዕለት ክስ አቅርበዋል። የቀረበባቸው ክስ የሶስት ሃገር ዜግነት በመያዝ የኬንያ ፓርላማ አባል ሆነዋል የሚል ነው።

በኬንያ የዜግነት ህግ መሰረት በመንግስታዊ ስልጣን ላይ የሚቀመጥ ኬንያዊ ቃለ መሃላ ከመፈጸሙ በፊት የሌለ ሃገር ዜግነቱን በይፋ እንዲተው ይገደዳል።

የ58 ዓመቷ ሶፍያ ሼክ አደን አየና በነሃሴ ወር በፓርላማ አባል ሆነው ስራ ሲጀምሩ ጥምር ዜግነታቸውን እንደያዙ የኢትዮጵያና የአሜርካ ዜግነታቸው ሳይተዉ ነበር ተብሏል።

በቀረበባቸው ክስ መሰረት ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ የፓርላማ አባልነታቸውን ያጣሉ በዚህም በፓርላማ አባልነታቸው በወር የሚያገኙትን 7ሺህ 330 የአሜሪካ ዶላር ወይንም 200ሺህ ያህል ብር ያጣሉ።