አንዲት የ13 አመት ታዳጊ ከተደፍረች በኋላ በተደፋባት አሲድ ሕይወቷ አለፈ

(ኢሳት ዲሲ–ነሐሴ 30/2010)አንዲት የ13 አመት ታዳጊ ከተደፍረች በኋላ በተደፋባት አሲድ መሰል ንጥረ ነገር ሕይወቷ አለፈ።

ጫልቱ አብዲ የተባለችውና ከምስራቅ ሐረርጌ በደኖ ወደ ሐረር መጥታ የቤት ሰራተኛ የነበረችው ይህች ታዳጊ የተደፈረችውና ሕይወቷ ያለፈው በአሰሪዋ እንደሆነም ተመልክቷል።

ስሙ ያልተጠቀሰው ይህ ግለሰብ ታዳጊዋን ከደፈራት በኋላ የአሲድ ጥቃት እንደፈጸመባትም ተመልክቷል።

ከጥቃቱም በኋላ በስቃይ ውስጥ እያለች በቤት ተደብቃ እንድትቀመጥ ማድረጉም ታውቋል።

ታዳጊዋ ከመሞቷ በፊት ለፖሊስ በሰጠችው መግለጫ እንዳመለከተችው ሰውነቷ መሽተት ሲጀምር ወደ ሆስፒታል ሊወስዳት ተገዷል።

በአዲስ አበባ የካቲት 12 ሆስፒታል በሕክምና ላይ እያለች ሕይወቷ ላለፈው የ13 አመቷ ታዳጊ ጫልቱ አብዲ ዛሬ በየካቲት 12 ሆስፒታል የሻማ ማብራት ስነስርአት ተካሂዶላታል።

ታዳጊዋን በመድፈርና በማቃጠል የተጠረጠረው ግለሰብ በቁጥጥር ስር የዋለ ቢሆንም እስካሁን ግን ፍርድ ቤት አለመቅረቡ ታውቋል።