አሜሪካ ፖሊሲዋን በመቀየር የአብይን መንግስት ማገዝ እንደሚገባት አንድ የአሜሪካ የስትራቴጂክ ጥናት ባለሙያ ተገናጉ

አሜሪካ ፖሊሲዋን በመቀየር የአብይን መንግስት ማገዝ እንደሚገባት አንድ የአሜሪካ የስትራቴጂክ ጥናት ባለሙያ ተገናጉ
( ኢሳት ዜና መስከረም 17 ቀን 2011 ዓ/ም ) የአሜሪካ ኢንተርፕራይዝ ኢንስቲቲዩት ዋና አጥኝ የሆኑት ኤሚሊ ኤስቴሊ “የኢትዮጵያ ስትራቴጂክ ፋይዳ” በሚል ርዕስ ለአሜሪካ ምክር ቤት የውጭ ጉዳይ ኪሜቴ ባወቀረቡት ጥናት ላይ እንዳስታወቁት፣ ኢትዮጵያ በሰብዓዊ መብቶች ዙሪያ መሻሻል በማሳየቷ እንዲሁም ከኤርትራ ጋር ያላትን ግንኙነት በማሻሻሏ የተስፋ ስሜቶችን ቢፈነጥቁም፣ በየጊዜው በሚታዩት የአካባቢ ግጭቶችና የውጭ ሃይሎች አካባቢውን ለመቆጣጠር በሚያደርጉት እሩጫ የተነሳ በአገሪቱ ከፍተኛ የሆነ አደጋ መደቀኑን ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ የሚታየው ፈጣን የፖለቲካ ለውጥ እና በተለያዩ አካባቢዎች የሚከሰቱት የብሄር ግጭቶች የአገሪቱን ሰላም አደጋ ውስጥ ጥለውታል። ጠ/ሚኒስትር አብይ አህመድ በወሰዱዋቸው የሰብአዊ መብት ማሻሻያ እርምጃዎች የህዝቡ ተስፋ ከፍ ብሎአል። ነገር ግን በዚያው ልክ የብሄር ግጭቶች ጨምረዋል። በኦሮምያና በሶማሊ ክልሎች በተፈጠረው ግጭት 130 ሺ ሰዎች ተፈናቅለዋል።
ተደጋጋሚ ግጭቶች መከሰታቸው አልሸባብ የኢትዮጵያ የሶማሊ ተወላጆችን በማሰባሰብ በኢትዮጵያ ላይ ጥቃት ሊፈጽም ይችላል። የአብይ መንግስት የሰብአዊ መብት አያያዙን እያሻሻለ በሚመጣም ዜጎችን በብዛት እያፈሰ ማሰሩና ኢንተርኔት ማፈኑ ይህን የተወሳሰብ ችግር የሚያባብሰው እንጅ የሚቀንሰው አይሆንም። የቀድሞ የጸጥታ አባላት በሶማሊ ክልል በሚፈጥሩት ችግር ተጨማሪ አለመረጋጋት ሊፈጠር እንደሚችል አጥኝዋ አመልክተዋል። ለረጅም ጊዜ በስልጣን ላይ የቆዩ ባለስልጣናትም በአገሪቱ የኢኮኖሚ እና የፖለቲካ ቀውስ በመፍጠር የዲሞክራሲ ሽግግር እንዳይካሄድ ሊያደርጉ ይችላሉ። አቢይ እየጨመረ የመጣውን የብሄር ፍጥጫ እያረገበ መምጣት ካልቻለ እንዲሁም ከመላው ኢትዮጵያ የተጣለበትን ከፍተኛ ተስፋ እውን ማድረግ ካልቻለ ከራሱ ወገን የሚያገኘውን ህዝባዊ ድጋፍ ሊያጣ ይችላል በማለት ጥናቱ አመልክቷል።
የኢትዮጵያ አለመረጋጋት አሜሪካ አልሸባብንና በሶማሊያ የሚገኘውን አልቃይዳን ለመቆጣጠር እንቅፋት ይፈጥርባታል። ኢትዮጵያም የውስጥ ጉዳዩዋን ለመፍታት በምትወስደው እርምጃ በአፍሪካ ህብረትና በአካባቢው ፖለቲካ ላይ የምትጫወተውን ሚና ይቀንሰዋል። በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የተጀመረው መልካም ግንኙነት ጥቅምና ጉዳቶችን ይዞ መምጣቱም በጥናቱ ተመልክቷል።
ኢትዮጵያ ከኤርትራ ጋር ያደረገችውን የሰላም ስምምነት ለመተግበር መወሰኗ የዲፕሎማሲ ግንኙነቱን ለመጀመር ቢረዳም፣ የኢትዮጵያ ወታደሮች አሁንም ከድንበር አካባቢ አልራቁም። የሁለቱም አገራት ግንኙነት አሁንም ጠንካራ የሚባል አይደለም። በኢትዮጵያ የጸጥታ ተቋማት ውስጥ ያሉ አክራሪዎች ግንኙነቱ እንዲሰናከል ሊያደርጉ ይችላሉ። የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ በጉዳዩ እጇን ማስገባቷም ሌላ ችግር ይዞ የሚመጣ ነው። በተባበሩት አረብ ኢሚሬትስ፣ በሳውድ አረቢያ፣ ካታርና ቱርክ መካከል ያለው ፉክክር የሶማሊ መንግስት እንዲዳከምና በአገሪቱም ሰላም እንዳይሰፍን እያደረገ ነው። ቻይናና ሩስያም እንዲሁ በአካባቢው ተጽዕኖዋቸውን ማሳረፍ ጀምረዋል። ኤርትራ ለሩስያ የጦር መርከቦች እቃ አቅርቦት የሚውል ግንባታ እንዲፈጸም ስምምነት መፈራረሙዋም በጥናቱ ተጠቅሷል። ኢትዮጵያ የኤርትራን ወደቦች መጠቀም ከጀመረች ሶማሊ ላንድና ጅቡቲ ገቢያቸው የሚቀንስ በመሆኑ ወደቦቻቸውን ለቻይናና ሩስያ ሊሰጡ ይችላሉ።
እነዚህ ሁሉ ችግሮች ባሉበት በኢትዮጵያ ዲሞክራሲያ ስርዓት እንዲገነባ እና የሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩ በማገዝ በአገሪቱ ዘላቂነት ያለው ሰላምና መረጋጋት በማምጣት አልሸባብና ሌሎችም አክራሪ ሃይሎችን መቆጣጠር ይቻላል። አሜሪካ የአብይ መንግስት በአገሪቱ ለሚነሱ የብሄር ግጭቶች ወታደራዊ አማራጭ እንዳይጠቀምና ሌሎች የግጭት መፍቻ መንገዶችን እንዲፈልግ እንዲሁም መሰረታዊ የሆኑ የመዋቅር ማሻሻያ ለውጦች እንዲደረጉ እገዛ ማድረግ ይገባታል። አሜሪካ በተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ ላይ ከመተማመን ይልቅ የራሱዋን ጥቅም ራሱዋ እንድታስከብርም ጥናቱ ሃሳብ አቅርቧል።