ትናንት ማምሻውን በደቡብ ወሎ ዞን በኮምቦልቻ ከተማ በ06 ቀበሌ በሚገኘው ደዌ ተቅዋ መስጂድ ግጭት ተፈጥሮ በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱ ተገለጸ።

ትናንት ማምሻውን በደቡብ ወሎ ዞን በኮምቦልቻ ከተማ በ06 ቀበሌ በሚገኘው ደዌ ተቅዋ መስጂድ ግጭት ተፈጥሮ በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱ ተገለጸ።
(ኢሳት ዜና ግንቦት 09 ቀን 2010 ዓ/ም) ምንጮቻችን ከሥፍራው እንደዘገቡት በእለቱ በስፍራው ለሶላት የመጡ ሙስሊሞች ለሁለት የተከፈሉ ሲሆን፣ የዚህም ምክንያቱ አብዛኛው ሙስሊም-የመንግስት ተላላኪዎች ናቸው የሚባሉትን” ፤ እናንተ የመንግሥት እንጅ የእስልምና ተወካይ ስላልሆናችሁ መስጂዳችንን መልሳችሁ ውጡልን!!” በማለት ተቃውሞ በማሰማቱ ነው።
ይህን ተከትሎ ጥያቄ ባነሳው ህዝብና መስጂዶቹን በመንግስት ችሮታ ተቆጣጥረውታል በሚባሉት ” አህባሾች” መካከል ለሠአታት የዘለቀ ግጭት መደረጉ ታውቋል።
በሰው ህይወትና በንብረት ላይ በውል ያልተገለጸ ጉዳት ያደረሰው በተኩስና በድንጋይ ውርወራ የታጀበው ይህ ብጥብጥ ከመግሪብ ሰላት ጀምሮ እስከ ምሽቱ ሁለት ሠአት ድረስ መዝለቁም ታውቋል።
” በህወሀት መራሹ ቡድን ሀይማኖታዊ ጣልቃ ገብነት ምክንያት እየተፈጠረ ያለው ቅራኔ በዚህ ከቀጠለ ከተማዋ የማያባራ ቀውስ መናኸሪያ መሆኗ ስለማይቀር አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ካቢኔ በዚህ ጉዳይ አስቸኳይ የመፍትሄ እርምጃ ሊወስዱ ይገባል ሲሉ የከተማዋ ነዋሪዎች ጥሪ ያቀርባሉ።
በህወኃት አገዛዝና በሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች መካከል ለተፈጠረው አለመግባባት አንዱና ዋነኛው ምክንያት፣ አገዛዙ በህገ መንግስቱ የተደነገገውን እና “መንግስት በሀይማኖት ጣልቃ አይገባም”የሚለውን አንቀጽ በመጣስ በአብዛኛው የሙስሊም ማህበረሰብ ላይ የማይፈልገውን አስተምህሮ ለመጫን መሞከሩ እንደሆነ ይታወቃል።