በኢትዮጵያ የኑሮ ውድነት ተባባሰ

(ኢሳት ዲሲ–ግንቦት 6/2010) በኢትዮጵያ የኑሮ ውድነት መባባሱ ተገለጸ።

ፋይል

በጤፍ፣ በበርበሬ፣ በዘይት፣ በስኳር፣በቲማቲምና በተለያዩ ምርቶች ላይ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ መታየቱን ኢሳት ወደ ተለያዩ ከተሞች በመደወል ካሰባሰበው መረጃ ለማወቅ ተችሏል።

በተለይም በከተሞች እየተባባሰ የመጣው የኑሮ ውድነት ህዝቡን እያማረረው መሆኑም ታውቋል።

መንግስት የኑሮ ውድነቱን ነጋዴዎችን ተጠያቂ በማድረግ እንደሚቀጣቸው ሲያስጠነቅቅ ነጋዴዎች ደግሞ ከውጭ ምንዛሪ ጋር የተያያዘ  እንደሆነ በመግለጽ የመንግስትን ወቀሳ ያጣጥላሉ።

በሌላ በኩል በዚህ ዓመት መንግስት ለብድር መክፈያ 16 ቢሊየን ብር እንደሚያወጣ ተገልጿል።

የአገሪቱ የብድር ጫና ከመካከለኛ ደረጃ ወደ ከፍተኛ ደረጃ ደርሷል ሲል አይኤምኤፍ ባለፈው ሳምንት ሪፖርት ማውጣቱ ይታወሳል።

ነጭ ጤፍ በአማካይ ከ2500 ብር እስከ 3000 ብር እየተሸጠ ነው።

ከ500 እስከ 1000 ብር ጭማሪ ማሳየቱን ነው የደረሰን መረጃ የሚያመለክተው።

በርበሬ የ70 ብር ጭማሪ ያሳየባቸው ከተሞች እንዳሉም ለማወቅ ተችሏል።

50ብር በአማካኝ ይሸጥ የነበረው በርበሬ 120 ብር ገብቷል።

በቀበሌ ከሚከፋፈለው ሌላ በየመደብሮች የሚሸጠው ዘይት ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ ማሳየቱም ታውቋል።

5ሊትር ዘይት 365ብር ደርሷል። 15 ብር ይሸጥ የነበረው ፉርኖ ዱቄት የ8ብር ጭማሪ አሳይቷል።

ስኳር ከቀበሌ ውጪ 1ኪሎ በ60ብር እየተሸጠ ሲሆን የ20ብር ጭማሪ እንደታየበትም ለማወቅ ተችሏል።

ቲማቲም የ7ብር ጭማሪ በማሳየት በ17 ብር እየተሸጠ ሲሆን አንድ ሊትር ወተት የወር ኪራይ 750 ብር መግባቱንም ከደረሰን መረጃ ለማወቅ ተችሏል።

ስጋ በኪሎ 170 ብር በመሸጥ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ ካሳዩት ምርቶች የሚጠቀስ ሆኗል።

በቆሎም እንዲሁ የ5ብር ጭማሪ እንደታየበት ለማወቅ ተችሏል።

በአጠቃላይ የኑሮ ውድነት ከዕለት ወደ ዕለት እየተባባሰ በመምጣቱ ህዝቡ በከፍተኛ ምሬት ላይ መሆኑን ለኢሳት በደረሰው መረጃ ላይ ተመልክቷል።

አንዳንድ ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች ቀደም ሲል ከነበረው አመጋገብ በጥራትና በመጠን ባነሰ ሁኔታ ለመመገብ መገደዳቸውንና የኑሮ ውድነቱ ከመሻል ይልቅ በየጊዜው እየናረ መምጣቱን በመግለጽ ከፍተኛ ችግር ውስጥ መግባታቸውን ነው የገለጹት።

መካከለኛ ኑሮ የሚኖረው ሰው በአሁኑ ጊዜ የድሃ ድሃ ደረጃ ውስጥ ገብቶ በኑሮ ውድነት እየተሰቃየ ነው የሚሉት የመረጃ ምንጮች ድሃ የነበረው ፈጽሞ ኑሮን መቋቋም አልቻለም ሲሉ ያለውን አስከፊ የኑሮ ሁኔታ ይገልጻሉ።

የህወሃት አገዛዝ ለኑሮ ውድነት ጣቱን እየቀሰረ ያለው በነጋዴዎች ላይ ሆኗል።

ስግብግብ ነጋዴዎች አላግባብ የዋጋ ጭማሪ ማድረጋቸውን ደርሼበታለሁ የሚለው የህወሃት አገዛዝ ርምጃ እንደሚወስድ አስጠንቅቋል።

ነጋዴዎች በበኩላቸው የዋጋ ግሽበትን ተከትሎ የተከሰተው የኑሮ ውድነት በተለያዩ ምክንያቶች የመጣ እንጂ በነጋዴው አይደለም ሲሉ ይሟገታሉ።

በተለይም የውጭ ምንዛሪ እጥረቱ ለኑሮው ውድነት ትልቅ ድርሻ መያዙን ነው ከነጋዴዎች አካባቢ የሚሰማው።

የኢኮኖሚ ባለሙያዎች እንደሚስማሙትም የውጭ ምንዛሪ እጥረቱ የዋጋ ግሽበትን በማስከተል የኑሮው ጫና በህዝቡ ላይ እንዲሆን አድርጎታል።

ይህ በቅርቡ የማይፈታ ይበልጡንም እየተባባሰ እንደሚመጣ ነው የዘርፉ ባለሙያዎች የሚገልጹት።

በሌላ በኩል የህወሃት መንግስት በዚህ ዓመት ለብድር ክፍያ 16 ቢሊየን ብር መመደቡ ታውቋል።

በእስከአሁን 11ቢሊየን ብሩ መከፈሉን የጠቀሰው ሪፖርተር ጋዜጣ ከእንግዲህ የአጭር ጊዜ ብድር እንዲቋረጥ መደረጉን ገልጿል።

ባለፈው ሳምንት ሪፖርት ያወጣው ዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ተቋም አይ ኤም ኤፍ የአገሪቱ የብድር ዕዳ መጠን በጠቅላላው ወደ 27 ቢሊዮን ዶላር መደረሱን አስታውቋል።

የአገሪቱ የብድር ጫናም ከመካከለኛ ደረጃ ወደ ከፍተኛ ደረጃ ደርሷል ሲልም ስጋቱን መግለጹ የሚታወስ ነው።