በአሁኑ ወቅት የኦሮሞ ነፃ አውጪ ነኝ በሚል ስም የጦርነት አዋጅ እያወጀ ያለው አካል ፣ እያደረገ ያለው ነገር እንዲያስብበት እና ወደትክክለኛው መንገድ እንዲመለስ ኦቦ ለማ መገርሳ አስጠነቀቁ።

በአሁኑ ወቅት የኦሮሞ ነፃ አውጪ ነኝ በሚል ስም የጦርነት አዋጅ እያወጀ ያለው አካል ፣ እያደረገ ያለው ነገር እንዲያስብበት እና ወደትክክለኛው መንገድ እንዲመለስ ኦቦ ለማ መገርሳ አስጠነቀቁ።
( ኢሳት ዜና ሃምሌ 4 ቀን 2010 ዓ/ም ) የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦቦ ለማ መገርሳ የጦርነት አዋጅ ያወጀውን ቡድን ያስጠነቀቁት፣ ትናንት በኦሮሚያ ምክር ቤት ባደረጉት ንግግር ነው።
“ከዚህ በፊት ቀጥታ ሲዋጉን የነበሩ አካላት ዛሬ ስፓንሰር በመሆንና ገንዘባቸውን በመርጨት የክልሉት ፀጥታ ለማደፍረስ እንቅልፍ አጥተው እየሰሩ ይገኛሉ ያሉት አቅቶ ለማ፣ ከስፓንሰሮቹ የሚለገሳቸውን ገንዘብ በመቀበል የተሰጣቸውን ተልዕኮ ለማስፈፀም ዝግጁ የሆኑ በርካታ የእኛው ወንድሞችም በመከላችን ይገኛሉ” ብለዋል፡፡
“ለዚህ ህዝብ ሁላችንም እንሥራለት በሚል ውሳኔ ሁሉም ወደ ሀገር ተመልሶ በሀሳብ በመፋለም አንድ ላይ መስራት አለብን ብለን ጥሪ ከማድረግም በላይ ፣ ህዝባችንን አምነን ብዙዎቹን ከሰሩት ወንጀልም ነፃ እንዲሆኑ አደረግን “ ያሉት ር ዕሰ መስተዳድሩ፣ የፓለቲካ ታርጋ ተለጥፎባቸው በሰው ሀገር የተበተኑ ወገኖቻችን ተመልሰው ለሀገር እንዲሰሩ በራፉን በከፈትንበት ፣ ብዙዎች ጥሪዎን ተቀብለው እየገቡ ባለበት፣ በሺዎች የሚቆጠሩ እስረኞችን እየፈታን ባለንበት እና አጠቃላይ የፓለቲካ ምህዳሩ እየሰፋ ባለበት ጊዜ ፣”አይ! የኦሮሞ ነፃነትን ለማስከበር ትክክለኛ የጦርነት መክፈቻው ጊዜ አሁን ነው” ተብሎ በኦሮሞ ህዝብ ስም የሚደረግ እንቅስቃሴ ትርጉሙ ምን እንደሆነ በግሌ አልገባኝ”ብለዋል።
አቶ ለማ አክለውም፦”ለኦሮሞ ነፃነት ለማስከበር የሚያስቡ ከሆነ ፣እስከዛሬ ይሄን ሁሉ ዘመን የት ነበሩ?…ሲሉ ጠይቀዋል።
. “ እነዚህ ወገኖች ከልጅ ፊት አባት ገድለው ሬሳውን አቃጥለዋል።ሬሳ በማቃጠል የህዝብ ነፃነት እንዴት መከበር እንደሚችል አላውቅም። ኦሮሞ-ኦሮሞን ነው እየገደለው ያለው።…በምዕራብ ኦሮሚያ እየሆነ ያለው ነገር ይሄ ነው፡፡” ሲሉም ርዕሰ መስተዳድሩ አክለዋል።
“ቄሮ ለዓመታት በመሪነት ባደረገው ትግልና በከፈለው መስዋዕትነት አሁን እያየነው ያለነው ለውጥ እንዲመጣ እና ዛሬ የመጣውን ውጤት እንድንጎናፀፍ አድርጎል.” ያሉት ኦቦ ለማ መገርሳ፣ “ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ በቄሮ ስም ለመነገድ የሚሞክሩ ወጣቶች እዚህም እዛም የመዝረፍና አንዳንድ አካባቢዎችን የማወክ አዝማሚያ እያሳዩ እንደሆነ አልሸሸጉም።
“ቄሮዎች ግን ይሄ በታሪክ ማህደር ላይ የተከተበ የጀግንነትና ለህዝብ መስዋዕትነት የከፈሉት ደማቸው ባክኖ እንዲቀርባቸው ስለማይፈልጉ፣ አሁንም እነዚህን ቅጥረኞች አደብ በማስገዛት እና ወደመስመር በማስገባት ረገድ ትልቅ ምሳሌ የሚሆን ስራ በመስራ ላይ ይገኛሉ”ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ “ህዝባችንም እንደዛው እያደረገ ነው፡ብለዋል።
ይህ ሕግን የማስከበርና ሰላምና መረጋጋትን የማረጋገጥ ተግባር በሁሉም አካባቢ ተጠናክሮና ተስፋፍቶ መተግበር እንዳለበትም አቶ ለማ አሣስበዋል፡፡
“በአሁኑ ወቅት በክልላችን መዋቅር ውስጥ እንደ ኦሮሚያ ፖሊስ ለህዝቡ ዋልታና መከታ የሆነ አካል አኔ በግሌ አላውቅም” ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ በዛ በጭንቀትና በመከራ እና አይዟችሁ የሚለን ባጣንበት ጊዜ ከጎናችን ቆሞ ደሙን እያዛራ እና ህይወቱን እየሰጠ ለዚህ ለዛሬው ቀን እንደንደርስ የሚችለውን ሁሉ ያደረገ የህዝብ አካል ነው”ብለዋል።
አቶ ለማ አክለውም፦”የኦሮሚያ ፓሊሶች ለሚከፈላቸው ደሞዝ አየይደለም ፋቲኩን የለበሱት፡፡ እኔ እንደ ኦሮሚየ ፓሊስ በቁርጠኝነት ለህዝብ የቆመ አላውቅም።ቁርስ በልቶ ምሳ ሳይደግም ፀሀይና ንፋስ እየተፈራረቀበት መካራውን በማየት ከገዛ ስንቁ ለህዝቡ እየቀነሰ ሲሰቃይ የነበረ የህዝብ ወገን ነው።ለህዝባቸው ሲሉ ቤተሰባቸውን በትነው በየቆላውና በየድንበሩ በርካቶቹ ህይወታቸውን አጥተዋል። …. ታዲያ እንዴት ዛሬ በኦሮሚያ ፓሊስ ላይ ልክ እንደህዝብ ጠላት ቦንብ ይጣልበታል…? ይህ ፖሊስ እንዴት ዛሬም ይገደላል……?ምን ተፈልጎ ነውአሁን አንዳችን በሌላችን ላይ ቂም እንድናወጣ ጥሪ እየተደረገ ያለው?”ሲሉ በአጽንዖት ጠይቀዋል።
“ኦሮሚያ ውስጥ አናርኪ ለመፍጠር ገንዘብ በመርጨት የሚሰራ ስራ አለ ። እንስራለን ብለን ያቀድነውን ስራ ትተን ሌላውን ስራ እድንሰራ ነው እየተፈለገ ያለው” ያሉት አቶ ለማ፣ …ዛሬም ችግሮች ቢኖሩም ቄሮዋች ከጎናችን ሆነው እየታገሉ ናቸው “ብለዋል።
አሁንም የኦሮሞ ነፃ አውጪ በሚል ስም የጦርነት አዋጅ እያወጀ ያለው አካል ድርጊቱን ቆም ብሎ እንዲያስቡበት እና ወደትክክለኛው መንገድ እንዲመለስ የመከሩት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ ይሄን ያሉት ለመንግስት ችግሩን መቆጣጠር ከባድ ሆኖበት ሳይሆን ወዳልተፈለገ የኃይል እርምጃ ከመግባት ይልቅ ጉዳዩ በሰላም እልባት እንዲያገኝ ካላቸው ፍላጎት በመነሳት እንደሆነ አብራርተዋል።ኦቦ ለማ መገርሳ ንግግራቸውን ሲቋጩም፦”ጭቆና መሸከም አንችልም ብለን ታግለንና መስዋእትነት ከፍለን ወደ ነጻነት መንገድ መሸጋገር ጀምረናል..ዛሬስ ነፃነትንም መሸከም የማንችል ህዝቦች ነን እንዴ..?”ሲሉ ጠይቀዋል።