በተለያዩ የኦሮምያ ከተሞች ለሁለተኛ ቀን በመካሄድ ላይ ያለው የስራ ማቆም አድማ በተጠናከረ ሁኔታ ቀጥሎአል

(ኢሳት ዜና የካቲት 6ቀን 2010ዓ/ም) በተለያዩ የኦሮምያ ከተሞች ለሁለተኛ ቀን በመካሄድ ላይ ያለው የስራ ማቆም አድማ በተጠናከረ ሁኔታ ቀጥሎአል
በአንዳንድ አካባቢዎች ወታደሮች በወሰዱት እርምጃ የሰዎች ህይወት ጠፍቷል።
ከዋና ከተማዋ አዲስ አበባ ተነስተው ወደ ተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሚጓዙ መንገደኞች በትራንስፖርት እጥረት መጓዝ ሳይችሉ ቀርተዋል። የንግድ እቃዎችን የጫኑ መኪኖች በየቦታው ቆመዋል።
በአዲስ አበባ ተቃውሞ ሊነሳ ይችላል በሚል ወታደሮች በተጠንቀቅ ቆመው ማንኛውንም እንቅስቃሴ ሲከታተሉ ውለዋል። ከሰዓት በኋላ ጀምሮ በዙሪያ ከተሞች ከፍተኛ ጭስ መታየቱን ተከትሎ የእሳት አደጋ ተሽከርካሪዎች ከተማውን አስጨንቀውት ውለዋል። የከተማ ህዝቡ ህንፃዎች ላይ ሆኖ የሚከናወነውን በተለያዬ ስሜት ውስጥ ሆኖ ሲከታተለው መቆየቱን ወኪላችን ገልጸዋል።
በለገጣፎ ፣ ሰንዳፋ፣ ወለቴና ሌሎችም የከተማዋ አቅራቢያ ከተሞች የተቃውሞ ሰልፎች የተደረጉ ሲሆን፣ ወጣቶች መንገዶችን ጎማ በማቃጠል ጭምር ዘግተዋል። ከአንፎ አካባቢ 42 ወጣቶች ተይዘው ካራ ፖሊስ ጣቢያ ከገቡ በሁዋላ ወደ ኮልፌ እስር ቤት ተዘውረዋል። ከካራ ቆሬ( ሃጂ አንባ) የተነሱ ወጣቶች ወደ መሃል አዲስ አበባ ጉዞ ሲያደርጉ በፖሊሶች ተበትነዋል።
በቢሾፍቱ እጅግ በርካታ ቁጥር ያለው ህዝብ ወደ አደባባይ በመውጣት ተቃውሞ ሲያካሂድ ቢውልም፣ የጸጥታ ችገር አልተፈጠረም። በአዳማ ፣ በአርሲ ፣ ሻሸመኔ፣ ኩየራ፣ ቀርሳ ኢላላ፣ ዶሌ፣ አዳባ፣ ዶዶላ፣ ኮምቦልቻ፣ ሀረር፣ መቱ፣ ሞያሌ፣ እና ሌሎችም በርካታ ቦታዎች የተቃውሞ ሰልፎችና የስራ ማቆም አድማዎች ተካሂደዋል። ትናንት ተቃውሞውን ያልተቀላቀሉት ቡሌ ሆራና ገርባ ከተሞች ዛሬ በመቀላቀላቸው ወደ ሞያሌ የሚካሄደው ጉዞ ሙሉ በሙሉ ተቋርጧል።
በሃረር ከተማ ከተለያዩ የገጠር አካባቢዎች የመጡ ወጣቶች ወደ መሃል ከተማ ሲገቡ ከሃረሪ ክልል ፖሊሶች ጋር ተገጭተዋል። ፖሊሶቹ በወሰዱት እርምጃ አንድ ሰው ሆስፒታል ከገባ በሁዋላ ህይወቱ አልፏል። ሌሎች ሁለት ሰዎችም ሳይገደሉ እንዳልቀሩ ወኪላችን ገልጿል። 10 ያክል የቄሮ መሪዎች ናቸው የተባሉ ወጣቶች በአገዛዚ ወታደሮች ተይዘው ውደ አልታወቀ ስፍራ ተወስደዋል። አርሶአደሩ ምርቱን ወደ ገበያ ለማቅረብ ፈቃደኛ ባለመሆኑ ከፍተኛ የአቅርቦት ችግር ተፈጥሯል።
ወደ ባህርዳርና ገንደር የሚወስደው መንገድ በፍቼና በሌሎችም ከተሞች በመዘጋቱ ከሰሜን የአገሪቱ ክፍል የተሰኑ መንገደኞች ለመመለስ ግድ ሆኖባቸዋል። ትናንት ምሽት የአጋዚ ወታደሮች ወጣቶችን እየደበደቡ ድንጋይ እንዲያነሱ ሲያስገድዱዋቸው ቢያመሹም፣ ወጣቶች ግን ተመልሰው መንገዶችን በመዝጋት ተቃውሟቸውን ገልጸዋል።
በድሬዳዋ ደግሞ የከተማዋ የቀበሌ ሰራተኞች በተዘጉ የንግድ ድርጅቶች ላይ ታሽጓል የሚል ወረቀት እየለጠፉ ነው።
በሌላ በኩል የክልሉ ም/ል የኮሚኒኬሽን ሃላፊ የሆኑት ወይዘሮ ኡሚ አባጀማል በባቱ፣ በለገጣፎና በጅማ 8 ሰዎች ጉዳት የደረሰባቸው መሆኑን እንዲሁም በሃረር ከተማ አማሬሳ ካምፕ ከሚገኙ ዜጎች የ4 ሰዎች በባሌ ዞን መደወላቡ ወረዳ ደግሞ 3 ሰዎች መገደላቸውን ተናግረዋል። የኢሳት ምንጮች እንደሚናገሩት ከሆነ ግን በሃረር የተገደሉት ዜጎች ቁጥር 11 ነው።
ኦህዴድ ተቃውሞው እንዲቆምና ህዝቡ ላነሳቸው ጥያቄዎች መልስ እንዲሰጥ ጊዜ እንዲሰጠው በም/ል ሊመንበሩ ዶ/ር አብይ አህመድ አማካኝነት ጥሪ አቅርቧል።
ከኦሮምያ ክልል ወጣ ስንል ደግሞ በደቡብ ክልል በከምባታ ዞን በሺንሺቾ ፣ በዱራሜ እና በሀደሮ ከተሞች የተቃውሞ ሰልፍ ሲካሄድ ውሎአል።