በምስራቅና በምዕራብ ጉጂ ዞኖች የተቃውሞ ሰልፎች ተካሄዱ

በምስራቅና በምዕራብ ጉጂ ዞኖች የተቃውሞ ሰልፎች ተካሄዱ
(ኢሳት ዜና ሚያዝያ 22 ቀን 2010 ዓ/ም) በአካባቢው ነዋሪዎች ዘንድ ከፍተኛ ተቃውሞ ሲቀርብበት የነበረው የሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ተጨማሪ የ10 አመት የኮንትራት ስምምነት ማግኘቱን ተከትሎ የአካባቢው ነዋሪዎች ስምምነቱን በመቃወም የተቃውሞ ሰልፍ አድርገዋል። በአዶላ ወዮ ተማሪዎች ወደ አደባባይ በመውጣት ስምምነቱን ተቃውመዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች የሚድሮክ ወርቅ ላለፉት 20 አመታት ከፍተኛ መጠን ያለው የወርቅ ማእድን ሲያወጣ ቢቆይም፣ ለአካባቢው ነዋሪዎች ያመጣው የህይወት ለውጥ የለም። ማእድኑ በሚረጨው ኬሚካል በርካታ ዜጎች አካል ጉዳተኞች መሆናቸውን የሚጠቅሱት ነዋሪዎች፣ መንግስት ኮንትራቱ እንዲራዘም ማድረጉ ህዝቡ ለአመታት ሲያቀርብ ለነበረው ጥያቄ ትኩረት እንዳልሰጠ የሚያሳይ ነው ይላሉ።
በምዕራብ ጉጂ ዞን ፊንጫ ከተማ በተደረገው ተቃውሞ ደግሞ ወታደሮች በተኮሱት አስለቃሽ ጭስ እስካሁን 3 ሰዎች ተጎድተው ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል። ከተጎዱት መካከል የአንደኛዋ ህይወት ከሰዓት በሁዋላ አልፏል።
የኦሮምያ የህዝብ ግንኙነት ቢሮ ሃላፊ የሆኑት አቶ አዲሱ አረጋ በፌስቡክ ገጻቸው ባወጡት ጽሁፍ በጉጂ ዞንም ሆነ በሻኪሶ የተነሳውን ተቃውሞ መንግስት በጥሞና እየተከታተለው መሆኑ ገልጸዋል። አቶ አዲሱ ህዝብና መንግስት በትብብር ችግሩን እንደሚፈቱት ከመገለጽ ውጭ ፣ መንግስት ችግሩን እንዴት እንደሚፈታው ወይም ህዝብ ጥያቄ አቅርቦ እያለ ለምን ስምምነቱን ለማሳደስ እንደፈለገ አልገለጹም። ኮንትራቱን ከማደሳቸው በፊት ከህዝብ ጋር መማከር እንደነበረባቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ።
የኦሮምያ የአካባቢ እንክብካቤና የማእድን ቢሮ ለሚድሮክ ላጋ ደምቢ የወርቅ ማእድን የኮንትራት ማራዘም ስምምነት እንዳይደረግለት አጥብቆ ተቃውሞ ነበር። እድሳቱ የአካባቢውን ህዝብ ጥያቄ እና የአካባቢ ጥበቃ መስፈርቶችን ያላሟላ ነው በማለት የድርጅቱ ሰራተኛ የሆኑት ዶ/ር ሃሰን የሱፍ ለማእድን ሚኒስቴር የተቃውሞ ደብዳቤ ጽፈው ነበር። ማእድን ሚኒስቴር በበኩሉ ሚድሮክ አስፈላጊውን የአካባቢ ጥበቃ መስፈርት የሚያሟላ በመሆኑ ፈቃዱ ይታደስለት የሚል አቋም ይዞ ተግባራዊ አድርጓል።