በሕጻናት ሞት ኢትዮጵያ ከግንባር ቀደም አምስት ሃገራት አንዷ መሆኗ ታወቀ

(ኢሳት ዲሲ–መስከረም 11/2011)በሕጻናት ሞት ኢትዮጵያ በአለም ላይ ከግንባር ቀደም አምስት ሃገራት አንዷ መሆኗን ተገለጸ።

የተባበሩት መንግስታት ተቋም እንዳስታወቀው   ባለፈው የምዕራባውያኑ አመት 2017 133ሺ ኢትዮጵያውያን ሕጻናት ሞተዋል።

የተባበሩት መንግስታት ኢንተር ኤጀንሲ ቡድን ከአለም ጤና ድርጅት፣ከተባበሩት መንግስታት አለም አቀፍ የሕጻናት ድንገተኛ ፈንድና ከአለም ባንክ የሰበሰባቸውን መረጃዎች መሰረት በማድረግ ባጠናቀረው ዘገባ በ2017 አመተ ምህረት የሞቱት 133ሺ ሕጻናት እድሜያቸው ከ5 አመት በታች ነው።

ከነዚህ ውስጥ 95ሺ የሚሆኑት አንድ ወር ሳይሞላቸው መሞታቸውም ተመልክቷል።

ለሕጻናቱ ሞት የተመጣጠነ ምግብና ውሃ እጦት፣መሰረታዊ ሕክምና አለማግኘት ምክንያት መሆናቸው ተመልክቷል።

ህንድ፣ናይጄሪያ፣ፓኪስታንና ኮንጎ በተመሳሳይ ከፍተኛ የሕጻናት ሞት የተመዘገበባቸው ሃገራት ሆነዋል።