በሕዝቦች ትግል የመጣው ለውጥ እንዳይቀለበስ መጠበቅ አለብን ተባለ

(ኢሳት ዲሲ–ጥቅምት 28/2011) በሕዝቦች ትግል የመጣው ለውጥ እንዳይቀለበስ የተገኘውን ተስፋ፥ ነፃነት እና ሰላም መጠበቅ እንደሚያስፈልግ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ገለጸ፡፡

ክልላዊ መንግስቱ በምዕራብ ጐንደር ዞን የተፈጠረውን ግጭት አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ እንዳለው በነጋዴ ባህር አካባቢ ማንነታቸው ለጊዜው ያልታወቁ ግለሰቦች ባደረሱት ጥቃት የ4 ሰዎች ህይወት ሊያልፍ ችሏል፡፡

በዚህ መነሻ በተፈጠረ ግጭት በዞኑ መተማ እና ሽንፋ አካባቢዎች ለጊዜው ቁጥራቸው ያልታወቁ ሰዎች ህይወትም መጥፋቱ ታውቋል። በንብረት ላይም ጉዳት ደርሷል፡፡

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ባወጣው መግለጫ እንዳለው በየአካባቢው የሚታዩ ግጭቶችን በሰከነና የህግ የበላይነትን አስጠብቆ መፍትሄ ለመስጠት አስተዳደሩና  ህዝብ እየሠሩ ይገኛሉ፡፡

በሰሞኑ በምዕራብ ጐንደር ዞን አዳኝ አገር ጫቆ ወረዳ ምስረታ በዓልን አክብረው እየተመለሱ ባሉ ወገኖች ላይ ማንነታቸው ለጊዜው ያልታወቁ ግለሰቦች ባደረሱት ጥቃት የ4 ሠዎች ህይወት ሊያልፍ ችሏል ነው ያለው፡፡

በዚህ መነሻ በተፈጠረ ግጭት በዞኑ መተማ እና ሽንፋ አካባቢዎች በሰው ህይወትና በንብረት ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡

እናም የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በግጭቱ ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የተሰማውን ጥልቅ ሃዘን ገልጿል፡፡

በሌላ በኩል አጋጣሚውን በመጠቀም ሁኔታውን በማባባስ ህዝብን ከህዝብ ለማጋጨት ጥረት እየተደረገ መሆኑን ነው የገለጸው።

ችግሩ ወደ ከፋ ግጭት እና ጥፋት ሳይሄድ አካባቢው እንዲረጋጋ ማድረግ ተችሏል ብሏል፡፡

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የፀጥታ ሃይሎች ከኢፌዲሪ መከላከያ ሠራዊት አባላት ጋር በመሆን በአካባቢው ችግሩን በቁጥጥር ስር ለማዋል እየሠሩ ይገኛሉም ነው ያለው፡፡  ጥፋተኞች በህግ ተጠያቂ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑንም ገልጿል።

እንደ መግለጫው በጉዳዩ ላይ ቀጥተኛ ተሣትፎ በማድረግ ችግሩ እንዲፈጠር ያደረጉ ተጠርጣሪ ግለሰቦችም በቁጥጥር ስር እየዋሉ ይገኛሉ፡፡

ይህንን የጥፋት ዓላማ ይዘው የሚንቀሳቀሱ አካላት እና የዚህ አስፈፃሚ ግለሰቦች ትርፋቸው ኪሣራ እንደሆነ ሊገነዘቡት ይገባል፡፡

የክልሉ ህዝብም የተገኘውን ሠላም እና ነፃነት በመጠበቅ ከመንግስት ጐን እንዲሰለፍ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ጥሪ አስተላልፏል፡፡

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በትግራይ ክልላዊ መንግስት የተሰነዘረበትን ወንጅላ በተመለከተ መልስ አልሰጠም።

የትግራይ ክልላዊ መንግስት ትላንት ባወጣው መግለጫ  የአማራ ክልል ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች በምዕራብ ጎንደር በማንነት ላይ ያነጣጠረ ጥቃት እንዲፈጸም ስላደረጉ ለሕግ እንዲቀርቡ መጠየቁ ይታወሳል።