ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ ከ33 አመታት በኋላ ኢትዮጵያ ገቡ

(ኢሳት ዲሲ–ታህሳስ 11/2011) የእርዳታ ማስተባበሪያና ማቋቋሚያ ኮሚሽን ኮሚሽነር የነበሩት ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ ከ33 አመታት በኋላ ኢትዮጵያ ገቡ።

          የደርግንመንግስት በመቃወም ስርአቱን ከከዱ ከፍተኛ ባለስልጣናት የመጀምሪያው የነበሩት ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በ1981 በኮለኔል መንግስቱሃይለማርያም ላይ የተካሄደው የመንግስት ግልበጣ ሙከራ ላይ ከውጭ ሆነው ተሳታፊ እንደነበሩም መረዳት ተችሏል።

          ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ ትላንት ከናሚቢያ ዊንዲሆክ አዲስ አበባ ሲደርሱ የመንግስት ባለስልጣናት እንዲሁም ቤተሰቦቻቸውና ወዳጆቻቸው እንደተቀበሏቸው ከመረጃው ለማወቅ ተችሏል።

          በአቀባበል ስነስርአቱ ላይ የቀድሞ መንግስት ምክትል ፕሬዝዳንት የነበሩት ኮለኔል ፍስሃ ደስታም መገኘታቸው ታውቋል።

          በአሜሪካ ኒዮርክ ከሚገኘው ኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ 2ኛ ዲግሪያቸውን አግኝተው ወደ ኢትዮጵያ እንደተመለሱ በደርግ መንግስት ውስጥ በተለያዩ የሃላፊነት ቦታዎች ያገለገሉት ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በ1979 ስርአቱን ጥለው በመውጣት፣በፕሪንስተን ዩኒቨርስቲ ውስጥ ሆነው የደም እንባ የተባለ መጽሃፍ በመጻፍ የስርአቱ ጉድፍ ያሉትን አጋልጠዋል።

          በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥ በቋሚ ተጠሪነት የኤርትራ ክፍለ ሃገር አስተዳዳሪነትና በእርዳታ ማስተባበሪያና ማቋቋሚያ ኮሚሽን ኮሚሽነርነት በደርግ ስርአት ውስጥ ማገልገላቸው ታውቋል።

          ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በ1981 የኮለኔል መንግስቱን መንግስት ለመገልበጥ በተደረገው ሙከራ ከውጭ ሆነው ተሳታፊ እንደነበሩም መረዳት ተችሏል።

          የኢትዮጵያ ወታደሮች ነጻ ንቅናቄን በመመስረት በግልበጣው ሒደት ተሳታፊ የነበሩት ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ መንግስት ከተገለበጠ በኋላ በሚደረገው ሒደት ውስጥ ሻዕቢያና ሕወሃት ተሳታፊ በሚሆኑበት መንገድ ላይ ከአቶ ኢሳያስ አፈወርቄና ከሕወሃት መሪዎች ጋር በወቅቱ መነጋገራቸውንም ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቆይታ መናገራቸው ይታወሳል።

          ለረጅም አመታት በተባበሩት መንግስታት ውስጥ በተለያየ የሃላፊነት ቦታ ያገለገሉት ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በአሁኑ ወቅት የአፍሪካ የሰላምና የጸጥታ ምርምር ተቋም የሚል ድርጅት ከሌሎች ባለሙያዎች ጋር በመመስረት በዋና ስራ አስፈጻሚነት እየመሩት እንደሚገኙም ለማወቅ ተችሏል።

          መቀመጫቸውን በአሁኑ ወቅት በናሚቢያ ዊንድሆክ ያደረጉት ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ ከ33 አመታት በኋላ ትላንት ማምሻውን ወደ ኢትዮጵያ ገብተዋል።

          ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ ትላንት ከናሚቢያ ዊንዲሆክ አዲስ አበባ ሲደርሱ የመንግስት ባለስልጣናት እንዲሁም ቤተሰቦቻቸውና ወዳጆቻቸው ተቀብለዋቸዋል።

          በአቀባበል ስነስርአቱ ላይ የቀድሞ መንግስት ምክትል ፕሬዝዳንት የነበሩት ኮለኔል ፍስሃ ደስታም መገኘታቸው ታውቋል።