ሬክ ማቻር የሰላም ስምምነቱን የመጨረሻ ምዕራፍ አልፈርምም አሉ

(ኢሳት ዲሲ–ነሐሴ 22/2010) የደቡብ ሱዳን አማጽያኑ መሪ ሬክ ማቻር የሰላም ስምምንቱን የመጨረሻ ምዕራፍ አልፈርምም ማለታቸው ተሰማ።

ይህን ተከትሎም በደቡብ ሱዳን ሰላም ለማስፈን የተጀመረው ጥረት ጥቁር ጥላ አጥልቶበታል ብሏል አፍሪካ ኒውስ በዘገባው።

በሬክ ማቻር በኩል እንደ ምክንያት የቀረበው የሰላም ስምምነቱ ለተቃዋሚዎች ዋስትናን አያረጋግጥም የሚል ነው።

በ2013 የተቀሰቀሰውና ከ10 ሺ በላይ ንጹሃን ዜጎች እልቂት ምክንያት ለሆነው የደቡብ ሱዳን የርስበርስ ግጭት ማብቂያ ይሆናል በሚል ተስፋ ተጥሎበት የነበረው የሰላም ስምምነት በሬክ ማቻር እምቢተኝነት ሊሰናከል ነው በሚል በርካቶች ስጋታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው።