ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከካራማራ ጦርነት ተሳታፊዎች ጋር ተወያዩ

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 6/2011) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በካራማራ ጦርነት የተሳተፉ ከቀድሞ የሰራዊቱ ተወካይ አባላት ጋር መወያየታቸው ተነገረ።

የሰራዊት አባላቱ የካራማራ ድልመንግስት ተገቢውን የታሪክ ትኩረት እና ክብደት እንዲሰጠው ጠይቀዋል።

የሃገርን ታሪክ አጥርቶ ለትውልድ ለማስጨበጥ እና ጠቃሚ ትምህርት ለመውሰድ ቅብብሎሹ በይዘቱ የተሟላ መሆን እንደሚገባው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ ተናግረዋል።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን ለካራማራ ድል መንግስት ተገቢውን የታሪክ ትኩረት እና ክብደት ይሰጠው የሚለው ጥያቄ ተገቢነት አለው ብለዋል።

በዕድሜ ዘመን ያካበቱትን የሃገርን ክብርና አንድነት የማስቀደም ብልሃት ለትውልዱ ልምዳቸውን እንዲያካፍሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ ለቀደምት የጦር ጀግኖች ጥሪ አቅርበዋል።

በውይይቱ በካራማራ ጦርነት ጊዜ በተለያዩ ወታደራዊ ሀላፊነቶች ላይ ያገለገሉት ሜጀር ጀኔራል መርዳሳ ሌሊሳ፣ ብርጋዴር ጄኔራል መስፍን ኃይሌ፣ ብርጋዴር ጀኔራል ካሳዬ ጨመዳ፣ ብርጋዴር ጄኔራል ዋሲሁን ንጋቱ  እና ሻለቃ ሽፈራው ወንድማገኝ መሳተፋቸው ታውቋል።