ሜ/ጄ ተክለብርሃን ወ/አረጋይ ይመሩት የነበረው ኢንሳ ከ10 ቢሊዮን ብር በላይ በሙስና ማባከኑ ታወቀ

ሜ/ጄ ተክለብርሃን ወ/አረጋይ ይመሩት የነበረው ኢንሳ ከ10 ቢሊዮን ብር በላይ በሙስና ማባከኑ ታወቀ
( ኢሳት ዜና ሃምሌ 3 ቀን 2010 ዓ/ም ) የዶ/ር አብይ አህመድን ጠ/ሚኒስትር ሆኖ መመረጥ አጥብቀው ሲቃወሙ፣ ጠ/ሚኒስትሩን “ጠላት” ብለው በመፈረጅ የለውጥ ሂደቱን ለመቀልበስ ጥረት እያደረጉ የሚገኙት የቀድሞው የኢንፎሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር የነበሩት ሜ/ጄኔራል ተክለብርሃን ወልዳረጋይ እና በአሁኑ ሰዓት በእስር ላይ የሚገኘው ምክትሉ ቢኒያም ተወልደ ከ200 በላይ የመንግስትን መስሪያ ቤቶችን የሚመለከቱ ፕሮጀክቶችን በመያዝ ከ10 ቢሊዮን ብር በላይ በሙስናና በተበላሸ አመራር ማባከናቸውን በድርጅቱ ላይ የተደረገ የጥናት ሪፖርት አመለከተ። ሁለቱም ግለሰቦች ለኢንሳ ውድቀትና ለጠፋው ገንዘብ ዋና ተጠያቂዎች መሆናቸው በጥናቱ ተመልክቷል።
ጄ/ል ተክልብርሃንና ቢኒያም “የሳይበር ሃይል ሄድኳርተር” ማቋቋሚያ ፕሮጀክት በሚል ሰበብ ኤጀንሲው በአዋጅ ከተቋቋመበት ዓላማ ውጭ የበርካታ የመንግስት መስሪያ ቤቶችን ስልጣንና ተግባር የሚወስድ፣ በርካታ ኤጀንሲዎች፣ ኢንስቲቲዩቶች፣ባለስልጣን ተቋማት እና ኢንተርፕራይዞችን በስሩ አቅፎ የሚይዝ እና የአገር ሉዓላዊነትና ህልውናን መጠበቅ በሚል ሰበብ የመንግስትን ሉዓላዊ ስልጣን ደረጃ በደረጃ በእጁ የሚያስገባ የአመራር ስርዓቱና መሪዎቹም ወታደሮች እንዲሆኑ የሚያስገድድ አዋጅ በ2009 ዓ.ም በኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር መሪነት ተረቆ ለመንግስት አቅርበው እንደነበር ጥናቱ ያመለክታል፡፡ “የሄድኳርተሩ” አደረጃትም በአገር ውስጥና በውጭ አገር እንደሚሆን ረቂቁ የሚያመለክት ሲሆን፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚኒስቴር ደረጃ የሚሾሙ አንድ ዋና አዛዥና ምክትሎች እንደሚኖሩት፣ ዋና አዛዡና ምክትሎች ሕገ- መንግስታዊ ታማኝነት፣ የብሄራዊ ደህንነትና ወታደራዊ ሳይንስና ጥበብ ዕውቀት ብቃት ያላቸውና ዘርፉን ጠንቅቀው የሚያውቁ እንደሚሆኑ በረቂቁ ተመልክቷል።
የሄድኳርተሩ ወይም ዋና ጽ/ቤቱ ሃላፊ ጀነራል መኮንኖች መሆን እንዳለባቸው በጥንቃቄ የተቀመጠ እና ዋና ዳይሬክተሩ ድርጅቱን ለመምራት አቅደው የነደፉት ሲሆን፣ በዋና ዳይሬክትሩ የሚመራ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ፣ ብሄራዊ ጂኦስፓሻል መረጃ ኤጀንሲ፣ ብሄራዊ ሳይበር ስታንዳርድ ኤጀንሲ፣ ብሄራዊ ሳይበር ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲቲዩት፣ ብሄራዊ ሳይበር ምርምርና ልማት ኢንስቲቲዩት፣ ብሄራዊ ሳይበር ኢንጂነሪንግ ኢንስቲቲዩት፣ ብሄራዊ ሳይበር ኦዲቲንግ፣ ግምገማና አክሪዴሽን ባለስልጣን፣ የመንግስት ሳይበር ልማት ኢንተርፕራይዞች የሚሉትን ተቋማት የማቋቋም እቅድ ነበራቸው።
በሳይበር-ሃይል ዋና ጽ/ቤት ዕዝና ቁጥጥር ስር እንዲሆኑ የተደራጁ ተቋማት የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ፣ የሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር፣ የመገናኛ እና ኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር፣ጂኦስፓሻል ኢንፎርሜሽን ኤጀንሲ፣ የሀገር መከላከያ ሚኒስቴር እና የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ተግባርና ሃላፊነቶችን የሚነኩ መሆኑን የጠቅላይ ዐቃቤ ህግ በቁጥር 01/ኤ-9/9/10 ጥር 30 ቀን 2010 ዓ.ም ለኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ የሳይበር – ሃይል ሄድኳርተር ለማቋቋም የተዘጋጀ ረቂቅ አዋጅን በማስመልከት በሰጠው የፅሁፍ አስተያየት ማመልከቱም በጥናቱ ተጠቅሷል።
የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ጄ/ል ተክለብርሃን ለመንግስት ያቀረቡት የሳይበር ሃይል ማዘዣ ጣቢያ ማቋቋሚያ አዋጅ ረቂቅ መፅደቁን ሳይጠብቁ፣ በተቋሙ ማዘዣ ጣቢያ ማቋቋም እና በውስጥ የተለያዩ ተቋማትን በማደራጀት ኃላፊዎችን የመሾም እና ሃብት በመመደብ ወደተግባራዊ ስራ ገብተው እንደነበር ጥናቱ ያሳያል፡፡
በዚህም በተቋሙ የውስጥ እና የውጭ መጠሪያ ያላቸው ተመሳሳይ ተቋም ሁለት ስያሜ ይዞ እንዲሰራና የተቋማት ኃላፊዎችም በውጭ በመንግስት የሚታወቅ፣ በውስጥ ደግሞ በተቋሙ ብቻ የሚታወቅና “ሄድኳርተር” ማቋቋምን ያለመ ማህተም አስቀርፀው ሲጠቀሙ እንደነበር ጥናቱ አመልክቷል፡፡
ባለፉት አምስት አመታት ኢንሳ 218 ፕሮጀክቶችን ከመንግስታዊ መስሪያ ቤቶች ተቀብሎ ሲሰራ ቢቆይም፣ የፕሮጀክቶች አፈጻጸም በአማካኝ 26.6% ብቻ ነው፡፡ በአንፃሩ ለፕሮጀክቶቹ ማስፈፀሚያ የሚሆነው አስር ቢሊየን ብር ሙሉ ለሙሉ ወጪ መደረጉ በጥናቱ ተረጋግጧል።
ከተያዙት ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ የሆነው “ዲጂታል ቴሌቭዥን ፕሮጀክት፣ ኢትዮጵያ ከአናሎግ ወደ ዲጂታል ቴሪስቴሪያል ቴሌቪዥን ስርጭት ለማሸጋገር በሚል የ 1 ቢሊዮን 392 ሚሊዮን 520 ሺ ብር በጀት በ2007 ዓ.ም አስፈቅዶ በ2009 ሙሉ በሙሉ ፕሮጀክቱን ለመጠናቀቅ ቃል የገባ ቢሆንም ስራው ግልጽነት በጎደለው መልኩ እየተሰራ መሆኑ፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያለውን አድማሳዊ የቴሌቭዥን ስርጭት ሽፋን ለማስፋት ተጨማሪ 26 አዳዲስ እና ሙሉ የዲቪቢ-ቲ2 ትራንስሚተሮች በተለያዩ የሀገራችን አከባቢዎች በማቋቋም የስርጭት ተደራሽነት ማስፋፋት፣ ብሔራዊ ማቀነባበሪያ ሄድ ኢንድ መሳሪያ ለመትከልና ለዚህም ሥራ የሚያስፈልግ መሰረተ ልማትና ግንባታ ማጠናቀቅ በእቅዱ ውስጥ የተካተቱ ስራዎች ቢሆኑም እስከ አሁን ድረስ አንድም የማሰራጫ ጣቢያ ሲስተም ተከላ ስራ አለመከናወኑ ታውቋል።
ለዲጂታላይዜሽኑ ብሔራዊ ማቀነባበሪያ እና መቆጣጠሪያ ማዕከል /ሄድ ኢንድ/ የግንባታ ሥራ በኮንትራክተሩ እና በፕሮጀክት ክትትል የአፈፃፀም ጉድለት ምክንያት በተያዘለት ጊዜ ባለመጠናቀቁ ስራው እንዲቋረጥ አማካሪው ድርጅቱ ባቀረበው የውሳኔ ኃሳብ መሰረት እንዲቋረጥ ተደርጓል፡፡ ፕሮጀከቱ በተበለው ጊዜ ዉስጥ ባይደርስም የኢንፎረሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ በየዓመቱ ለአራት ዓመታት በጀቱን ሲጠቀምበት ቆይቷል፡፡ የወጣው ወጪና የተሰራው ሥራ ሲመዘን ፕሮጀክቱ ከተቀመጠለት የጊዜ መርሃ ግብር አንፃር የማይመጣጠን መሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡
በአሁኑ ሰዓት ለሄድ ኢንድ የተባለው ህንፃ ግንባታ ሙሉ በሙሉ የተቋረጠ ሲሆን፣ ፕሮጀክቱ ለወደፊትም ለማስቀጠልና አጠናቆ ለተፈለገው ዓላማ ለማዋል ውስብስብ ችግሮች ያሉበት ነው፡፡
ሌላው ፕሮጀክት “ ኢትዮሳት የሳተላይት ፕላትፎርም ፕሮጀክት” ሲሆን፣ ኤጀንሲው ወጪ ቆጣቢ፣ ጥራቱን የጠበቀ እና ደህንነቱ የተረጋገጠ ብሔራዊ የተቀናጀ የዲጂታል ሳተላይት ቴሌቭዥን ኘላትፎርም አቀርባለሁ በሚል የተጀመረ ነው፡፡ ፕሮጀክቱ ከዩተልሳት እና ኤስ ኢ ኤስ ከተባሉ የውጭ ኩባንያዎች የሳተላይት ባንድ ዊድዝ ግልጽ ባልሆነ መንገድ በመከራየት የመንግስትና የግል ሚዲያዎች በዚህ የኪራይ ሳተላይት እንዲጠቀሙ በማስገደድ የውጭ ምንዛሪ አስቀራለሁ ብሎ ለመንግስትና ህዝብ የተሳሳተ መረጃ እንዲደርስ አድርጓል፡፡ ይሁን እንጅ ምንም አይነት የሴኩሪቲ እሴት በተቋሙ ሳይጨመር፣ የሳተላይት ኦፕሬተሮች በግልፅ ሳይወዳደሩ፣ የውጭ ምንዛሬ ሳያስቀርና ወጪ ቆጣቢ አካሄድ ሳይከተል፣ ጥራቱን ባልጠበቀና የሚዲያ ተቋማትን ፍላጎት በማይመልስ ባንድዊድዝ እንዲጠቀሙ በማድረግ የአገልግሎት ጥራት እንዲጓደል አድርጓል፡፡
በዚህ ዝቅተኛ አገልግሎት ለዩተልሳት ኩባንያ በጠቅላላ 4,200,000.00 የአሜሪካ ዶላር ወይም ብር 114,780,844.47 እንዲሁም ለኤስ ኢኤስ ኩባንያ በጠቅላላው 1,481,798.32 የአሜሪካ ዶላር ወይም ብር 40,568,589.82 በድምሩ ለሁለቱ ኩባንያዎች 5,681,798.32 የአሜሪካ ዶላር ወይም ብር 155,349,434.29 የተከፈለ ሲሆን፣ ወጪ ቆጣቢ የተባለው የመጀመሪያው ዕቅድ በትክክል ያልተጠና እና መንግስትና ህዝብ ከኤጀንሲው ከሚጠብቁት ተልዕኮ ውጪ ሲፈጽም መቆየቱን ለማወቅ ተችሎአል። ሁለቱም የሳተላይት ኩባንያዎች ለኢሳት አግልግሎት ሲሰጡ ቆይተው በመጨረሻ ከመንግስት ጋር ስምምነት ሲፈራረሙ ኢሳትን አናስተናግድም ማለታቸው ይታወቃል፡፡
በእነዚህና በሌሎችም በርካታ ፐሮጀክቶች ከፍተኛ የሆነ የሃገር ሃብት መባከኑን ከጥናቱ ለመረዳት ይቻላል። በ2009 ዓ.ም የፌደራል ዋና ኦዲተር ባደረገው አመታዊ የኦዲት ምርመራ የፋይንንስና ሪሶርስ አስተዳደራቸው ግልፅነት የሌላቸው ወይም ዲስክለይመር በሚል የመጨረሻው ዝቅተኛ ደረጃ ከተቀመጡት ጥቂት የመንግስት ተቋማት አንዱ ሁኖ መቀመጡ በጥናቱ ላይ ተጠቅሷል።