ለአቶ ገዱ አንዳርጋቸው የክብር ዶክትሬት ሊሰጥ ነው

(ኢሳት ዲሲ–ሃምሌ 5/2010)የሃሮማያ ዩንቨርስቲ ለአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው የክብር ዶክትሬት ሊሰጥ ነው፡፡

ዩኒቨርሲቲው ለአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ገዱ አንዳርጋቸው እና ለመሃመድ አህመድ ቆጴ የክብር ዶክትሬት እንደሚሰጥም ለአማራ ብዙኃን መገናኛ ድርጅት መረጃ ሰጥቷል፡፡

ሃሮማያ ዪኒቨርሲቲ በተለያዩ መርሐ ግብሮች ከመጀመሪያ እስከ ሶስተኛ ዲግሪ ያሰለጠናቸውን ከ 7900 በላይ ተማሪዎች ሐምሌ 07/2010 ዓ.ም እንደሚያስመርቅ ታዉቋል፡፡

በዕለቱም ለርዕሰ መስተዳድር ገዱ አንዳርጋቸው እና ለመሃመድ አህመድ ቆጴ የክብር ዶክትሬት ይሰጣቸዋል፡፡

የሃሮማያ ዩንቨርስቲ ለአማራ ክልል ርእሰመስተዳድር አቶ ገዱ አንድአርጋቸው የክብር ዶክትሬት ለመስጠት የወሰነው በኢትዮጵያ እየተደረገ ባለው የለውጥ እንቅስቃሴ እያደርጉ ላለው አስተዋጽኦ እውቅና ለመስጠት ነው።

መሃመድ አህመድ ቆጴ የመጀመሪያው የኦሮምኛ ቋንቋ ጋዜጠኛ ሆነው በሃረር ከተማ ይሰሩ እንደነበረም ከዩኒቨርሲቲው ካገኘነው መረጃ አረጋግጠናል፡፡

ሀረማያ ዩኒቨርሲቲ ከዚህ በፊት ለሁለት ሰዎች ብቻ ነው የክብር ዶክትሬት የሰጠዉ፡፡

በማሽላ ላይ ታዋቂ ተመራማሪ እና የምግብ እና የእርሻ ድርጅት/FAO/ አማካሪው ፕሮፌሰር ጋቢሳ እጄታ እና የጅቡቲው ፕሬዝዳንት እስማኤል ኦማር ጌሌ  በዩኒቨርሲቲው የእስካሁን ታሪክ የክብር ዶክትሬት የተሰጣቸዉ ናቸው፡፡

በቅርቡም የጅማ ዩንቨርስቲ ለኦሮሚያው ፕሬዚዳንት አቶ ለማ መገርሳ የክብር ዶክትሬት መስጠቱ ይታወሳል።