ሁለት የሕወሃት አባላት ከሃላፊነታቸው ተነሱ

(ኢሳት ዲሲ–ነሐሴ 7/2010) በአዲስ አበባ መስተዳድር ለረጅም አመታት በከፍተኛ ሃላፊነት ላይ የነበሩ ሁለት የሕወሃት አባላት ከሃላፊነታቸው ተነሱ።

የአዲስ አበባ ከተማ ስራ አስኪያጅ እንዲሁም በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የሕዝብ ግንኙነት አማካሪ በመሆን ከ10 አመታት በላይ በስልጣን ላይ የቆዩት ሁለቱ ግለሰቦች ከስልጣናቸው የተነሱት በሳምንቱ መጨረሻ እንደሆነም ተመልክቷል።

የአዲስ አበባ መስተዳድር ምክትል ከንቲባ በቅርቡ የስልጣን ብወዛ ሲያደርጉ ከሃላፊነት የተነሱት ሁለቱ የሕወሃት ባለስልጣናት የከተማዋ ስራ አስኪያጅ አቶ ሃይሌ ፍሰሃና በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የሕዝብ ግንኙነት አማካሪው አቶ ተወልደ ገብረጻድቅ ናቸው።

ሪፖርተር ጋዜጣ ምንጮቹን ጠቅሶ ባቀረበው በዚህ ዘገባ እንዳመለከተው አቶ ተወልደ ገብረጻድቅ የአዲስ አበባ ኢህአዴግ ጽሕፈት ቤት ሊቀመንበር በመሆንም በከተማዋ ፓርቲውን በበላይነት ሲመሩ ቆይተዋል።

ሁለቱን ግለሰቦችን በመተካትም አዳዲስ ሰዎች ተሹመዋል።